ቀጥታ፡

በጎንደር ከተማ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ለሥርዓተ ምግብ መሻሻል ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው

ጎንደር፤ ነሐሴ5 /2018 (ኢዜአ) ፡-በጎንደር ከተማ የተተገበረው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ለሥርዓተ ምግብ መሻሻልና ለሥራ እድል ፈጠራ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ የእንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት መምሪያ አስታወቀ።

የመምሪያ ኃላፊው አቶ መላኩ ደምሌ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በጎንደር ከተማ የተተገበረው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ለሥርዓተ ምግብ መሻሻልና ለሥራ እድል ፈጠራ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው።


 

በከተማው የሚገኙ ቀበሌዎችን በሥጋ፣ በወተት፣ በማር፣ በዶሮና በሌሎች የልማት ዘርፎች በኩታ ገጠም በማደራጀት ወደ ሥራ መገባቱን አውስተዋል።

በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ108 ሚሊዮን ሊትር በላይ የወተትና እስከ 65 ሚሊዮን የሚደርስ የእንቁላል ምርት ማምረት መቻሉን ገልጸዋል።

የእንቁላል ምርቱም የአካባቢውን የገበያ ፍላጎት ከመድረስ ባለፈ ወደ ሱዳን ጭምር በመላክ የአምራቾችን ተጠቃሚነት ማሳደግ መቻሉን ተናግረዋል።

በተለይም የወተት ምርታማነትን ለማሳደግ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የላሞች ዝርያ ማሻሻል በመሰራቱ፣ በቀን ከአንድ ላም በአማካይ የሚገኘውን ወተት 42 ሊትር ማድረስ ተችሏል ብለዋል።

በ2018 በጀት ዓመት ለ8 ሺህ 790 ወጣቶች በዘርፉ አዲስ የሥራ እድል መፈጠሩን አስረድተዋል።

የከተማዋ ነዋሪ የሆኑት አቶ አያልነው ማሩ እንደገለጹት፤ በዘመናዊ የወተት ከብቶች እርባታ ላይ በመሰማራታቸው ለውጥ ማምጣት ችለዋል። 

ሥራውን በሦስት ላሞች የጀመሩት አቶ አያልነው፣ አሁን ላይ ከ80 በላይ ላሞች ማድረስ መቻላቸውን ጠቁመው በቀን እስከ 400 ሊትር ወተት በማምረት እያቀረቡ እንደሚገኙ አስረድተዋል። 

በላም እርባታና ወተት ማምረት ሥራውም እስከ 25 ለሚሆኑ ቋሚና ጊዜያዊ ሰራተኞች የሥራ እድል መፍጠር መቻላቸውን ተናግረዋል።


 

ሌላኛው የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የእንስሳት ሕክምና መምህር ዶክተር ካሳሁን በሬ በበኩላቸው፤ ከመደበኛ ሥራቸው ጎን ለጎን ከ2009 ዓ.ም ጀምሮ በዶሮ እርባታ ዘርፍ በመሰማራት ውጤታማ መሆናቸውን ገልጸዋል። 

አሁን ላይ ለ10 ሰዎች በቋሚና በጊዜያዊነት የሥራ እድል መፍጠራቸውን ጠቁመው፣ ወደ ዘርፉ ለሚቀላቀሉ ሌሎች ወጣቶች ነፃ የሙያ ድጋፍ እየሰጡ እንደሚገኙም አስረድተዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም