የኢትዮጵያ ዲጂታል የመሶብ አገልግሎት የአፍሪካ ሀገራት በተሞክሮነት የሚጋሩት የመንግሥት አገልግሎቶች ማሳለጫ መሳሪያ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ ዲጂታል የመሶብ አገልግሎት የአፍሪካ ሀገራት በተሞክሮነት የሚጋሩት የመንግሥት አገልግሎቶች ማሳለጫ መሳሪያ ነው
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ዲጂታል የመሶብ አገልግሎት የአፍሪካ ሀገራት በተሞክሮነት የሚጋሩት የመንግሥት አገልግሎቶች ማሳለጫ መሳሪያ መሆኑን የኢፌዴሪ መሶብ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዮናስ አለማየሁ ገለጹ::
ተቀማጭነታቸውን በአዲስ አበባ ያደረጉ የተለያዩ ሀገራት አምባሳደሮች፣ በኢፌዴሪ መሶብ አገልግሎት የሚሰጡ የአንድ ማዕከል፣ የተንቀሳቃሽና የተቀናጀ መሶብ ዲጂታል አገልግሎቶችን ጎብኝተዋል።
የኢፌዴሪ መሶብ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዮናስ አለማየሁ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፣ የመሶብ ዲጂታል አገልግሎት በአጭር ጊዜ ውስጥ ዜጎች ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት የሚያገኙበትን ዕድል ፈጥሯል።
ይህም ብልሹ አሠራርንና የመልካም አስተዳደር ውስንነቶችን በመቅረፍ፣ በመንግሥትና በዜጎች መካከል በአገልግሎት አሰጣጥ ረገድ ያለው መተማመን እንዲጎለብት እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
በተለይም የተበታተኑ የመንግሥት አገልግሎቶች በአንድ ማዕከልና በተቀናጀ አግባብ የሚመሩበትን ወሳኝ ዕድል በመፍጠር፣ የተገልጋዮችን እርካታ እያሳደገ እንደሚገኝ ተናግረዋል።
በአዲስ አበባ የተጀመረው የኢፌዴሪ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት አሁን ላይ በተንቀሳቃሽና በተቀናጀ የዲጂታል አገልግሎት ተደራሽነቱ በእጅጉ መስፋፋቱን አስረድተዋል።
የመሶብ አገልግሎትም የመንግሥት አገልግሎት ሥነ-ምኅዳር ውጤታማነትን በማሻሻል፣ እመርታዊ ውጤት እንዲመጣ እያደረገ እንደሚገኝ አብራርተዋል።
የመሶብ ዋነኛ ዓላማ የዜጎችን የአገልግሎት እርካታ ማሳደግ መሆኑን በመጠቆም፣ ከመሶብ አገልግሎት ጋር በተያያዘ ከ98 በመቶ በላይ የዜጎች የአገልግሎት እርካታ በማስመዝገብ ከፍተኛ ውጤት ማምጣቱን ጠቁመዋል።
በቀጣይም በፌዴራል፣ በክልሎችና በከተማ አስተዳደሮች እየተስፋፋ የሚገኘውን የመሶብ አገልግሎት ተደራሽነት የበለጠ በማጠናከር፣ የዜጎችን አገልግሎት ለማሳለጥ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል።
በስምንት ተቋማት ከ40 በላይ አገልግሎቶች የተጀመረው የመሶብ አገልግሎት፣ በአሁኑ ወቅት በአንዱ ማዕከል ብቻ ከ27 በላይ ተቋማት የሚሰጡትን ከ288 በላይ አገልግሎቶች እያቀረበ መሆኑን አስታውቀዋል።
መሶብ ዲጂታል የመንግሥት አገልግሎት “ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ” ሽግግርን በማፋጠን፣ በቴክኖሎጂ የታገዘ የአገልግሎት ሥርዓት አካል ሆኖ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ዲጂታል የመሶብ አገልግሎት ሌሎች የአፍሪካ ሀገራት በተሞክሮነት የሚቀስሙት የመንግሥት አገልግሎቶችን ማሳለጫ ተምሳሌታዊ አብነት መሆኑንም አስረድተዋል።
ተቀማጭነታቸውን በአዲስ አበባ ያደረጉ የሀገራት አምባሳደሮችም፣ ኢትዮጵያ በመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ያስመዘገበችውን እመርታዊ ውጤት፣ ልምድና ተሞክሮ እንዲቀስሙ ያለመ መሆኑን አንስተዋል።
ይህም ዲፕሎማሲያዊ ትስስርን ለማጠናከር፣ ልምድ ለመለዋወጥና የትብብር ዕድሎችን ለመፍጠር ያለመ መሆኑን አስረድተዋል።
የመሶብ ሥራ ገና በመጀመሪያ ምዕራፍ ያለ ሲሆን፣ በቀጣይ የአገልግሎቶችን ቁጥር ማሳደግ፣ ዲጂታላይዜሽንን ማፋጠን፣ የመሶብ አገልግሎትን በሁሉም ከተሞችና ወረዳዎች ማስፋፋት እና ልምዱን ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ማካፈል ቀጣይ ትኩረቶች ይሆናሉ።