ቀጥታ፡

ኦዲተሮች ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን በመተግበር ለሂሳብ ሪፖርቶች ጥራት መጠበቅ በቁርጠኝነት ሊሰሩ ይገባል

አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ) ፦ ኦዲተሮች ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን በመተግበር ለሂሳብ ሪፖርቶች ጥራት መጠበቅ በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሂሳብ አያያዝ እና ኦዲት ቦርድ አመለከተ።

ቦርዱ በኦዲት ጥራት የግምገማ ውጤቶች ዙሪያ ከኦዲተሮች ጋር እየተወያየ ይገኛል።

የኢትዮጵያ ሂሳብ አያያዝ እና ኦዲት ቦርድ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍቃዱ አጎናፍር በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ኦዲተሮች ለሂሳብ ሪፖርቶች ጥራት መጠበቅ በቁርጠኝነት ሊሰሩ ይገባል።

የሂሳብ ሪፖርቶችን ጥራት የሚያስጠብቁ ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን ጠብቆ መስራት ላይ ውስንነቶች መኖራቸውን የግምገማ ውጤቱ እንደሚያመላክት ጠቁመው ኦዲተሮች ይህንን ክፍተት ለመሙላት ሊሰሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። 

ነጻ እና ገለልተኛ ሆኖ በሃላፊነት መስራት ከኦዲተሮች የሚጠበቅ ሌላው ሙያዊ ግዴታ መሆኑን ጠቁመው የስነ ምግባር መርሆዎችን ጠብቆ መስራት እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል።  

ጥራቱን የጠበቀ የሂሳብ ሪፖርት ኢንቨስትመንት ለመሳብ፣ ለታክስ ስርአት ውጤታማነት እንዲሁም ለሀገር ኢኮኖሚ መሳለጥ ትልቅ ሚና እንዳለውና ለስኬታማነቱ የኦዲተሮች ሙያዊ ደረጃዎችን ጠብቆ መስራት ቁልፍ ድርሻ አለው ብለዋል።

እንደ ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ ገለጻ፤ ኢትዮጵያ ወደ ካፒታል ገበያ ስርአት እየገባች በመሆኑ ጥራትና ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የኦዲት ስርአት አስፈላጊ ነው።

የኢትዮጵያ ሂሳብ አያያዝ እና ኦዲት ቦርድም የኦዲተሮችን አቅም በመገንባት ለዘርፉ ውጤታማነት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። 

የውይይት መድረኩ በኦዲት ጥራት ክፍተቶች ዙሪያ በመመካከር የጋራ መፍትሔ ለማመላከት መሆኑን ጠቁመዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም