ቀጥታ፡

በሀገሪቱ እየተመዘገበ ያለውን የኢኮኖሚ እድገት ቀጣይነት ለማረጋገጥ በትብብርና በቅንጅት መስራት ይገባል

ጋምቤላ፤ ነሐሴ 2/2018 (ኢዜአ) ፦ የኢንቨስትመንቱን ዘርፍ በማጠናከር እንደ ሀገር እየተመዘገበ ያለውን የኢኮኖሚ እድገት ቀጣይነት ለማረጋገጥ የትብብርና የቅንጅት ስራዎች ሊጠናከሩ እንደሚገባ የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ ዓለሚቱ ኡሞድ ገለጹ።

በሀገር አቀፍ ደረጃ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በተከናወኑት ሥራዎች ከ4 ነጥብ 44 ቢሊዮን  የአሜሪካን ዶላር በላይ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት መሳብ መቻሉን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን አስታውቋል።

የፌዴራል፣ የክልልና የከተማ አስተዳደሮች የኢንቨስትመንት አስፈጻሚዎች የጋራ ሀገራዊ የምክክር መድረክ ዛሬ በጋምቤላ ከተማ መካሄድ ጀምሯል።


 

ርዕሰ መስተዳድሯ በዚሁ ወቅት  እንዳሉት፤ እንደ ክልል ብሎም እንደ ሀገር ሰፊ የኢንቨስትመንት አማራጮች አሉ፤ እነዚህንም ልማት ላይ ማዋል ይገባል።

በዚህም  እየተመዘገበ ያለውን የኢኮኖሚ እድገት ቀጣይነት ለማረጋገጥ በፌዴራልና በክልሎች የተጀመሩ የትብብርና ቅንጅታዊ አሠራሮች ይበልጥ ሊጠናከሩ ይገባል ብለዋል።

በክልሉ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በኢንቨስትመንት ዘርፉ በተከናወኑት ሥራዎች በርካታ ባለሀብቶች ወደ ክልሉ በመግባት በዘርፉ እየተሳተፉ እንደሚገኙና ተጨባጭ ውጤትም  እየተመዘገበ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

በቀጣይም በክልሉ ያሉትን የግብርና፣ የማዕድን፣ የቱሪዝምና ሌሎች የኢንቨስትመንት አማራጮች  ምቹ በማድረግ ለዘርፉ መጠናከር የክልሉ መንግሥት በትኩረት እንደሚሠራ ነው ያረጋገጡት።

የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ዳጋቶ ኩምቤ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፤ ኮሚሽኑ የተጣለበትን ሀገራዊ ኃላፊነት ለመወጣት ባከናወናቸው ተግባራት አበረታች ውጤቶችን እያስመዘገበ ይገኛል።


 

በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በዘርፉ በተከናወኑት ሥራዎች ከ4 ነጥብ 44 ቢሊዮን  የአሜሪካን ዶላር በላይ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት መሳብ መቻሉን ጠቁመዋል።

ይህም ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር  ሲነጻጸር ከ8 ከመቶ በላይ ብልጫ ያለው መሆኑን ገልጸዋል።

በበጀት ዓመቱ አበረታች ውጤቶችን ማስመዝገብ የተቻለው የፌዴራልና የክልል ባለድርሻ አካላት ያደረጉት ያልተቆጠበ የተቀናጀ ጥረት ውጤት መሆኑንም ተናግረዋል።

በቀጣይም የትብብርና የቅንጅታዊ ሥራዎችን በማጠናከር በዘርፉ የተገኙትን ስኬቶች ይበልጥ ለማስፋት እንደሚሠራ ምክትል ኮሚሽነሩ ገልጸዋል።

የጋምቤላ ክልል ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሎው ኡቡፕ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በክልሉ ባሉት የኢንቨስትመንት አማራጮች የባለሀብቶች ተሳትፎ እንዲጠናከር በማድረግ ረገድ ውጤታማ ሥራዎች ተከናውነዋል ብለዋል።


 

በቀጣይም ከምክክር መድረኩ የሚገኙ ተሞክሮና ልምዶችን በማስፋት ለዘርፉ ውጤታማነት በትኩረት እንደሚሠራ ተናግረዋል።

ከዛሬ ጀምሮ ለሁለት ቀናት በሚቆየው የምክክር መድረክ የፌዴራል፣ የክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች የኢንቨስትመንት አስፈጻሚዎች በ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸምና በአዲሱ በጀት ዓመት ዕቅድ ዙሪያ በመወያየት የጋራ አቅጣጫ ያስቀምጣሉ ተብሎ ይጠበቃል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም