ቀጥታ፡

በተያዘው በጀት ዓመት ከማዕድን ዘርፍ 6 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ለማግኘት ታቅዷል

አዲስ አበባ ፤ ሐምሌ 30/2018 (ኢዜአ) ፦ በ2019 በጀት ዓመት ከማዕድን ዘርፍ 6 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ለማግኘት መታቀዱን የማዕድን ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ተገኝ ገለጹ።

ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የ2018 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸም እና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ ላይ ግምገማ አካሄዷል።

የማዕድን ሚኒስትሩ ኢንጂነር ሀብታሙ ተገኝ በወቅቱ የማዕድን ዘርፍ ከአምስቱ የሀገሪቱ ዋና ዋና የኢኮኖሚ ምሰሶዎች አንዱ መሆኑን ገልጸው፣ ባለፉት ዓመታት የዘርፉ ዕድገት ከጊዜ ወደ ጊዜ በፍጥነት እየጨመረ መምጣቱን አመላክተዋል።

በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከዘርፉ 5 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ማግኘት መቻሉን ገልጸዋል፡፡

ኢትዮጵያ የተፈጥሮ ጋዝ ለመጀመሪያ ጊዜ ማውጣት የጀመረችበት በተጠናቀቀው በጀት አመት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

የተፈጥሮ ጋዙ በአሁኑ ወቅት ለትላልቅ የሴራሚክ ፋብሪካዎች በግብዓትነት እየዋለ እንደሚገኝና ወደፊትም ለትራንስፖርት፣ ለማዳበሪያ ምርትና ለኃይል ማመንጫነት እንደሚውል አስረድተዋል።

በበጀት ዓመቱ የማዳበሪያና የብረት ማቅለጫ ፋብሪካዎች ሥራ መጀመራቸውን ተናግረው፤ እንደ ፖታሽ ያሉ ስትራቴጂካዊ ማዕድናትን ወደ ምርት ለማስገባት ዝግጅቶች እየተደረጉ መሆኑን አመላክተዋል፡፡

በክልሎች በአነስተኛ ደረጃ ላሉ የማዕድን ሥራዎች ፈቃድ እንዲሰጡ ሥልጣን መውረዱ ለዘርፉ ዕድገት ትልቅ አስተዋጽኦ ማድረጉን ገልጸዋል።

ዘርፉ በበጀት ዓመቱ ከ200 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉንም እንዲሁ።

በ2019 በጀት ዓመት ከማዕድን ዘርፍ 6 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ለማግኘት ታቅዶ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አመላክተዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም