ቀጥታ፡

በምዕራብ ጎንደር ዞን በመኸር እርሻ 546 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለምቷል

ገንዳውኃ፣ ሐምሌ29/2018 (ኢዜአ):- በምዕራብ ጎንደር ዞን በመኸር እርሻ546 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች መልማቱን  የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። 

በዞኑ ግብርና መምሪያ የሰብል ልማት ባለሙያ አቶ ሞገስ ጋሹ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በምርት ዘመኑ በዞኑ ከ529 ሺህ 650 ሄክታር በላይ መሬት በዘር ለመሸፈን ታቅዶ ወደ ሥራ ተገብቷል።

በተደረገው ከፍተኛ ርብርብም እስካሁን ባለው ሂደት ከእቅድ በላይ ከ546 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የተለያዩ ሰብሎችን ማልማት እንደተቻለ ተናግረዋል።

ከዚሁ ውስጥ ከ98 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው መሬት በባለሀብቶች የለማ ሲሆን፣ ቀሪው ደግሞ በአርሶ አደሮች መሸፈኑን ገልጸዋል።

አኩሪ አተር፣ ማሽላ፣ ሰሊጥ፣ ጥጥ፣ ማሾና ሌሎች ሰብሎች በብዛት የለሙ መሆናቸውንም አመልክተው፤ በምርት ዘመኑ ከለማው መሬት ከ12 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ተናግረዋል።

የተጀመረው እምቅ የልማት እንቅስቃሴ እስከ ምርት ስብሰባ ድረስ ተገቢው ክትትልና ድጋፍ እንደሚደረግለት ጠቁመዋል።

በዞኑ በእርሻ ኢንቨስትመንት ከተሰማሩ ባለሀብቶች መካከል አቶ አብርሃም ድንቁ እንዳሉት፤ በዘንድሮው ዓመት ግብዓት እና የባለሙያ ድጋፍን በወቅቱ በማግኘታቸው የልማት ሥራዎችን በስፋት ማከናወን አስችሏቸዋል። 

በዚህም 200 ሄክታር መሬት በጥጥ፣ ማሽላ፣ አኩሪ አተርና ሰሊጥ ማልማታቸውን አመልክተው፤ ሰብሉ በጥሩ ቁመና ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል። 

ትራክተሮችንና ሌሎች የግብርና ሜካናይዜሽን መሣሪያዎችን በስፋት በመጠቀማቸው ያቀዱትን መሬት በፍጥነት በዘር ለመሸፈን እንደቻሉም አብራርተዋል።

በመተማ ወረዳ በግብርና ሥራ የሚተዳደሩት አርሶ አደር ብርሃኑ ጌታሁን በበኩላቸው፤ በመኸር እርሻው 15 ሄክታር መሬታቸውን ሙሉ ለሙሉ ማልማታቸውን ገልጸዋል።

"የዝናብ ወቅቱን ጠብቀን በኩታ ገጠም አሰራር ነው መሬታችንን ያረስነው" ያሉት አርሶ አደሩ፤ የዝናብ ሥርጭቱን መሠረት ያደረገ የተባይና አረም ቁጥጥር እያደረጉ መሆናቸውን ተናግረዋል። 

አሁን የተዘራው ሰብል ተስፋ ሰጪ በመሆኑ የተሻለ ምርት  እንደሚጠብቁም ገልጸዋል።

በዞኑ ባለፈው የ2017/18 የምርት ዘመን 525 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለምቶ ከ10 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደተገኘ ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም