የመደመር መንግሥት የዲጂታል መሠረተ ልማት እመርታ የዜጎችን ተጠቃሚነት እያሳለጠ ነው - ብሩክ ታዬ (ዶ/ር) - ኢዜአ አማርኛ
የመደመር መንግሥት የዲጂታል መሠረተ ልማት እመርታ የዜጎችን ተጠቃሚነት እያሳለጠ ነው - ብሩክ ታዬ (ዶ/ር)
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 28/2018 (ኢዜአ)፦ የመደመር መንግሥት በዲጂታል መሠረተ ልማት ያስመዘገበው እመርታ የዜጎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያሳለጠ መሆኑን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ብሩክ ታዬ (ዶ/ር) ገለጹ።
የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም (ፋይዳ) በመንግሥት የልማት ድርጅትነት እንደገና ተደራጅቶ "ፋይዳ ቨርስ ዲጂታል ሶሉሽንስ ኢንተርፕራይዝ" በሚል ስያሜ በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ሥር ተካቷል።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በተገኙበት በኢትዮጵያ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ጉዞ አዲስ ምዕራፍ የከፈተው የ"ፋይዳ ቨርስ" ይፋዊ የሥራ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ተካሂዷል።
የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ብሩክ ታዬ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ ፋይዳ ቨርስ የኢትዮጵያን የዲጂታል ዘመን ጥንካሬ፣ ዘላቂነትና በዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ያጎለብታል ብለዋል።
ባለፉት ስምንት ዓመታት የመደመር መንግሥት የቴሌኮሙኒኬሽን መሠረተ ልማትን በማጠናከር በድምፅና በኢንተርኔት አገልግሎት ተጠቃሚዎችን ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ ማሳደጉን ገልጸዋል።
የፌዴራል፣ የክልልና የከተማ አስተዳደሮች መሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎቶችም የመንግሥትን አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነት እያሳደጉ መሆናቸውን ተናግረዋል።
የፋይዳ አገልግሎት በአፍሪካ ከፍጥነት የዲጂታል ማንነት ሥርዓቶች አንዱ እየሆነ ነው ያሉት ዋና ሥራ አስፈፃሚው፤ ፋይዳ ቨርስ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስን መቀላቀሉም ተቋማዊ ጥንካሬን ይፈጥራል ብለዋል።
የኢትዮጵያ የሕዝብ መሠረተ ልማት የዲጂታል ቴክኖሎጂ አቅምና ልምድም ደኅንነቱ የተጠበቀ የዲጂታል ማንነት ሥርዓት በመገንባት በአፍሪካም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ትኩረት እየሳበ መሆኑን አንስተዋል።
የፋይዳ ቨርስ ዲጂታል ሶሉሽንስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ዮዳሄ አርዓያሥላሴ በበኩላቸው፤ በጥቂት ዓመታት ውስጥ የዜጎችን ማንነት በዲጂታል መንገድ የመመዝገብና የማረጋገጥ ሰፊ ሥራ መከናወኑን ገልጸዋል።
የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም በአዲስ መልክ "ፋይዳ ቨርስ ዲጂታል ሶሉሽንስ" በሚል ወደ የመንግሥት የልማት ድርጅት ማደጉም የዲጂታል ውጤታማነትን የበለጠ ለማጎልበት የተወሰደ ስትራቴጂያዊ እርምጃ መሆኑን አስረድተዋል።
ተቋማዊ ሽግግሩም በራስ አቅም የቴክኖሎጂ ፈጠራንና ዘላቂ የፋይናንስ መሠረትን በማጣመር ወደ ተሻለ የዲጂታል አገልግሎትና የንግድ ሥርዓት ለመሸጋገር የተዘጋጀ ስትራቴጂያዊ አቅጣጫ መሆኑን ገልጸዋል።
በዲጂታል ማንነት መሠረተ ልማት የተፈጠረው አቅም ለፈጠራ፣ ለኢንቨስትመንት፣ ለፋይናንስ አካታችነትና ለዘመናዊ የመንግሥት አገልግሎቶች ጠንካራ መሠረት እንደሚሆንም አመልክተዋል።