በክልሉ የከተሞችን እድገትና የገጠር የልማት ሽግግር ዘላቂነት ታሳቢ ያደረገ ፕላን በማዘጋጀት እየተተገበረ ነው - ኢዜአ አማርኛ
በክልሉ የከተሞችን እድገትና የገጠር የልማት ሽግግር ዘላቂነት ታሳቢ ያደረገ ፕላን በማዘጋጀት እየተተገበረ ነው
ባህር ዳር፤ሐምሌ 28/2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል የወቅቱን የከተሞችን እድገትና የገጠር የልማት ሽግግር ዘላቂነት ታሳቢ ያደረገ ፕላን በማዘጋጀት እየተተገበረ እንደሚገኝ የክልሉ ፕላን ኢንስቲትዩት ገለጸ።
የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ምትኩ ዓለማየሁ (ዶ/ር) ዛሬ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳሉት፤ በክልሉ ከተሞችና የገጠር ቀበሌዎች መጪውን እድገትና የሕዝብ አኗኗር መሠረት ተደርጎ እየተሠራ ነው።
ከተሞች ካላቸው ፈጣን እድገት ጋር ተያይዞ ዘላቂነት ያለው የመሠረተ ልማት ግንባታ፣ የመኖሪያ አካባቢዎች፣ ማህበራዊ አገልግሎት የሚሰጡ ተቋማትንና ሌሎችንም ሁኔታዎች ባሟላ መንገድ መጪውን ጊዜ ታሳቢ በማድረግ በፕላን እንዲመሩ እየተደረገ ይገኛል።
እንዲሁም የገጠር ሽግግርን የተሳካ ለማድረግ የገጠር ቀበሌ ማዕከላት በፕላን ላይ መሠረት አድርገው እንዲቋቋሙ በቅንጅት እየተሠራ እንደሆነም አንስተዋል።
በተለይም የኮሪደር ልማት ኢኒሼቲቭ፣ ከተሞችና የገጠር አካባቢዎች በዘላቂ ፕላን እንዲመሩ አስገዳጅ ከመሆኑም በላይ ለዘላቂ እድገት መልካም ሆኖ መገኘቱን ተናግረዋል።
ኢንስቲትዩቱ በ2018 በጀት ዓመት ተቋማዊ ሪፎርም ከማድረግ ባሻገር ለአሠራር የሚያግዙ የሕግ ማሻሻያዎችን የማድረግ ሥራ ተሠርቷል ብለዋል።
እንዲሁም 137 የተለያየ ዓይነት ፕላን በማዘጋጀት ወደ ትግበራ እንዲገባ መደረጉን ጠቅሰው፤ ከእነዚሁ ውስጥ 37 የሚሆኑት የገጠር ቀበሌ ማዕከላት ፕላኖች መሆናቸውን ገልጸዋል።
በፕላን ዝግጅቱ ከ14 ሺህ በላይ የሕብረተሰብ ክፍሎችን ማሳተፍ መቻሉን ጠቅሰው፤ የፕላን ትግበራ፣ ክትትልና ቁጥጥር ሥራ መካሄዱንም አብራርተዋል።
ኢንስቲትዩቱ በ2019 በጀት ዓመትም 187 የተለያየ ዓይነት ፕላን ለማዘጋጀት አቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን ጠቅሰዋል።
የፕላን ዝግጅቱ የክልሉን የ25 ዓመት አሻጋሪ የልማትና የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ መሠረት በማድረግ እየተተገበረ እንደሚገኝ ተናግረዋል።
ከሚዘጋጀው ፕላን ውስጥም 130 ያህሉ የገጠር ቀበሌ ማዕከላት መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ይህም መንግሥት ለገጠር ሽግግር የሰጠውን ትኩረት መሠረት በማድረግ የሚሠራ ነው ብለዋል።
የገጠር ማዕከላቱ የመኖሪያ አካባቢዎችን፣ መሠረተ ልማትን፣ የገበያ ቦታዎችን፣ ማህበራዊ አገልግሎት መስጫ ተቋማትንና የአርሶ አደሩን የግብርና ሥራ በሚያሳልጥ አግባብ የሚሠሩ መሆናቸውን ገልጸዋል።
ተዘጋጅተው የሚቀርቡ ፕላኖች ወደ ትግበራ ሲገቡ በየደረጃው የሚገኝ አመራርና ባለሙያ ሕብረተሰቡን በማሳተፍ መተግበር እንዳለበትም ዋና ዳይሬክተሩ አሳስበዋል።