አረንጓዴ ዐሻራ የኢትዮጵያን አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ዕውቅና በማሳደግ የዜጎች የሀገራዊ ልማት ባህል እየሆነ ነው - ኢዜአ አማርኛ
አረንጓዴ ዐሻራ የኢትዮጵያን አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ዕውቅና በማሳደግ የዜጎች የሀገራዊ ልማት ባህል እየሆነ ነው
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ዕውቅና በማሳደግ የዜጎች የሀገራዊ ልማት ባህል እየሆነ መምጣቱን የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) ገለጹ።
የዘንድሮው "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሃሳብ የሚካሄደው የ800 ሚሊዮን የአንድ ጀምበር የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ዛሬ ሐምሌ 27/2018 ዓ.ም ከማለዳው 12፡00 ሰዓት ጀምሮ በመላ ሀገሪቱ ተካሄዷል።
የፕላንና ልማት ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማት አመራርና ሠራተኞች በአንድ ጀምበር የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በአዲስ አዳማ ፈጣን መንገድ ዳርቻ የአረንጓዴ ዐሻራቸውን አኑረዋል።
የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የአየር ንብረት ለውጥን በመቋቋምና የአፈርና የውሃ ሀብት ጥበቃን በማጠናከር ዘርፈ ብዙ የኢኮኖሚ ፋይዳ እያስገኘ ነው።
ይህም የኃይል ማመንጫ ግድቦችን ለደለል ተጋላጭነት ከመቀነስ ባለፈ የኤሌክትሪክ ኃይልን ዘላቂነትና የምግብ ዋስትናን የሚያጠናክር አቅም እየፈጠረ መሆኑን አብራርተዋል።
በዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብርም የሚኒስቴሩና ተጠሪ ተቋማት አመራርና ሠራተኞች ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬ ችግኞችን መትከላቸውን ገልጸዋል።
መርሃ ግብሩም የኢትዮጵያን የአቮካዶና ሌሎች የፍራፍሬ ምርቶች ወጪ ንግድ ምርታማነትን በማሳደግ ለሥራ ዕድል ፈጠራና ለውጭ ምንዛሬ ግኝት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አንስተዋል።
የዜጎችን የይቻላል መንፈስ በማጎልበትም ኢትዮጵያ በአፍሪካና በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና እያተረፈች መሆኗን ገልጸዋል።
የሕዝቡ ከፍተኛ ተሳትፎም አብሮነትና አንድነትን በማጠናከር የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የሀገራዊ የልማት ባህል እንዲሆን እያስቻለ መሆኑን አንስተዋል።
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ዕውቅና በማሳደግ የዜጎች የሀገራዊ ልማት ባህል እየሆነ መምጣቱንም አስረድተዋል።
የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ጀሚላ መሀመድ በበኩላቸው፤ በዛሬው ዕለት በሚኒስቴሩና ተጠሪ ተቋማቱ የተተከሉት የፍራፍሬ ችግኞች አርሶ አደሩን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ናቸው ብለዋል።
ህብረተሰቡ በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ለታቀደው ግብ ስኬት ችግኞችን በመትከልና በመንከባከብ የበኩሉን ሚና እንዲወጣም ጥሪ አቅርበዋል።