ቀጥታ፡

የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር ለኢትዮጵያ የቱሪዝም ዘርፍ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ ነው

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር ለኢትዮጵያ የቱሪዝም ዘርፍ ዕድገትና ለካርበን ልቀት መቀነስ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታዎች ገለጹ፡፡

የኢትዮጵያ ቱሪዝም ሚኒስቴርና የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ከተጠሪ ተቋማቱ ጋር በመሆን በአንድ ጀምበር የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር አሻራቸውን አኑረዋል፡፡

የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ ስለሺ ግርማ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ችግኝ መትከል ለቱሪዝም ዘርፍ ዕድገት መሠረት መጣል ነው፡፡


 

በዱር እንስሳት ጥበቃ ስፍራዎችና በብሔራዊ ፓርኮች ውስጥ ያለውን የደን ሽፋን እንዲጨምር በማድረግ በኩል ከፍተኛ ሚና እንዳለው ገልጸዋል፡፡

መርሃ ግብሩ የዱር እንስሳትን ስደት ከመቀነስ ባሻገር የፓርኮችን የቱሪስት መስህብነት በከፍተኛ ደረጃ በማሳደግ ጎብኚዎች ከተፈጥሮ ጋር የሚገናኙበትን፣ ንጹህ አየርና አረንጓዴ አካባቢን የሚመርጡበትን የዘላቂ ቱሪዝም ዕድል ያሰፋል ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ የምታሳየው የተግባር ምላሽ ዓለም አቀፍ ገጽታዋን በበጎ በመቀየር በዘላቂና በአረንጓዴ ቱሪዝም አርአያ እንድትሆን ማስቻሉን ገልጸዋል፡፡

የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ሀሰን መሀመድ በበኩላቸው፤ መርሃ ግብሩ የኢትዮጵያውያንን አንድነት በተግባር ያሳየበት ታሪካዊ ክስተት ነው ብለዋል፡፡


 

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት የተጀመረው ይህ ንቅናቄ ኢትዮጵያን በአየር ንብረት ጥበቃ አርዓያ እና የዓለም አቀፍ የችግሮች መፍትሄ አካል ያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል።

የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የካርበን ልቀትን መቀነስ ቀዳሚ ግቡ መሆኑን በማንሳት፤ አረንጓዴ ዐሻራ በአንድ በኩል የምድርን ጸጋ መጠበቅ በሌላ በኩል ደግሞ የአየር ብክለትን የመከላከል ሚና እንዳለው ተናግረዋል፡፡

ባለፉት ዓመታት የተተከሉ የቡና፣ አቮካዶ እና የፍራፍሬ ችግኞች ለቤተሰብ የገቢ ምንጭ፣ ለሀገር ደግሞ የውጭ ምንዛሬ መሳቢያ መሆን ጀምረዋል ብለዋል፡፡

የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል፣ የበረሃማነት መስፋፋት በመግታትና እና ለውሃ እጥረት ምላሽ በመስጠት ለነገው ትውልድ የተሻለች ሀገር ማስረከብም እንደሚያስችል ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም