ቀጥታ፡

በጅማ ዞን በመኸር እርሻው 930 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ዘር ተሸፍኖ እየለማ ነው

ጅማ፤ ሐምሌ 25/2018(ኢዜአ)፦ በጅማ ዞን በመኸር እርሻው 930 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ዘር ተሸፍኖ እየለማ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ።

የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ ቲጃኒ ተማም ለኢዜአ እንደገለጹት በዞኑ በ2018/19 ምርት ዘመን መኸር ወቅት ለሰብል ምርትና ምርታማነት እድገት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው።

በመኸር እርሻው 883 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ዘር በመሸፈን 36 ሚሊየን ኩንታል ምርት ለማግኘት ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን ተናግረዋል።

እስካሁን በተደረገ ጥረት ከእቅድ በላይ 930 ሺህ ሄክታር መሬት ታርሶ በበቆሎ፣ በጤፍ፣ በሩዝ እና በሌሎች ሰብሎች ዘር ኘሸፈኑን ገልጸዋል።


 

በዘር ከተሸፈነው ውስጥ 200ሺህ ሄክታሩ በበቆሎ ዘር መሸፈኑን ጠቁመው ቀድሞ የተዘራ በመሆኑም አሁን ላይ በጥሩ ቁመና ላይ እንደሚገኝ ተናግርዋል።

በምርት ወቅቱ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በተሰጠው ትኩረት አብዛኛው ሰብል በኩታ ገጠም የተዘራ መሆኑን አመልክተዋል።

በዞኑ ከሚገኙ የግብርና ግብዓት ማዕከላትና ዩኒየኖች ጋር በመቀናጀትም የግብርና ግብዓቶችን በተሳካ መልኩ ማሰራጨት መቻሉንና ለአርሶ አደሩ እየተደረገ ያለው የክትትልና ሙያዊ ድጋፍ ተጠናክሮ መቀጠሉን አስታውቀዋል።

በዞኑ ሊሙ ኮሳ ወረዳ በግብርና ልማት ከተሰማሩ ወጣቶች መካከል ሚልኮ ሙዲን ዓምና በቆሎን ከሌሎች የአካባቢው ወጣቶችና አርሶ አደሮች ጋር በክላስተር በማልማት የተሻለ ምርት ማግኘቱን አስታውሷል።

በዘንድሮ ምርት ዘመንም ቀደም ብሎ የመሬት ዝግጅት በማድረግና አስፈላጊውን የግብርና ግብዓት በመጠቀም የዘራውን በቆሎ እየተንከባከበ መሆኑን ተናግሯል።

ሌላው የወረዳው አርሶ አደር ጌታቸው አሊ በበኩላቸው ዘንድሮ በቆሎን በስፋት መዝራታቸውንና የበቆሎ ምርጥ ዘር በወቅቱ በማግኘታቸው የዘር ስራውን በወቅቱ ለማከናወን ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው አስረድተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም