ቀጥታ፡

በዞኑ የማር ምርት አቅርቦትና ተጠቃሚነት አድጓል

መቱ ፤ ሐምሌ 23/2018(ኢዜአ)፦ በዞኑ የማር ምርት ቴክኖሎጂ፣ አቅርቦትና ተጠቃሚነት ማደጉን የኢሊባቦር ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ።

የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አወል መሐመድ  ለኢዜአ እንደገለጹት ፤ባለፉት አምስት ዓመታት ለማር ምርት  በተሰጠው ትኩረት በዘርፉ ለውጥ ለማምጣት ተችሏል።


 

በዋናነትም ዘመናዊ ቀፎና ለስራው የሚያስፈልጉ ተያያዥ ቴክኖሎጂዎችን በስፋት በማዳረስ ዘርፉን ለማሳደግ በተደረገው ጥረት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልፀዋል።

ይህን ተከትሎም ከአምስት ዓመታት በፊት በዞኑ ከ5 ሺ ቶን የማይበልጥ የነበረው ዓመታዊ የማር ምርት መጠንን ወደ 20 ሺ ቶን ከፍ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል።

በመስኩ በቀፎ ማምረት ስራ ተደራጅተው የተሰማሩትን ጨምሮ ለአርሶ አደሮችና በማር ንግድ ለተሰማሩ ዜጎች ሰፊ የስራ ዕድል መከፈቱንም ተናግረዋል።

በዞኑ በቾ ወረዳ ከ8 ሺ በላይ አርሶ አደሮችና ማሕበራት በንብ ማነብና የማር ምርት ተሰማርተው እንደሚገኙ የገለጹት ደግሞ የወረዳው ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ተስፋዬ ዲቤሳ ናቸው።


 

ጽህፈት ቤቱ ለዘመናዊ ቀፎ አቅርቦት በሰጠው ትኩረትም ከ50 ሺህ በላይ ቀፎዎችን ለማሕበራትና አርሶ አደሮች ማቅረብ መቻሉን ገልፀዋል።

በወረዳው የማር ምርት ልማት ላይ ከተሰማሩ አርሶ አደሮች መካከል ወይዘሮ አይናለም ጌታቸው፤ በ12 ቀፎዎች የጀመሩትን የማር ምርት ወደ ሃምሳ ቀፎ ማሳደጋቸውን ነው የሚናገሩት።


 

በማር ምርቱ የቤተሰብ  ፍጆታን ከመሸፈን ባለፈ በዓመት እስከ ሶስት መቶ ኪሎ ግራም  ለገበያ እንደሚያቀርቡ ተናግረዋል።

ወጣት ሻቡ አብዱራህማን እና ጓደኞቹ በበኩላቸው፤ በማሕበር ተደራጅተው በማር ምርት በመሰማራት ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል።

በመስኩ ጠንክረው በመስራት ራሳቸውን ከመቻል ባለፈ የስራ እድል  ለመፍጠር ጠንክረው እየሰሩ መሆኑንም ገልጸዋል።

በኢሉባቦር ዞን በአጠቃላይ ከ70 ሺ በላይ አርሶ አደሮች በንብ ማነብና በማር ምርት ልማት ተሰማርተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም