በክልሉ በሁሉም ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት የተሻለ የኢኮኖሚ እድገት ማስመዝገብ ተችሏል - ኢዜአ አማርኛ
በክልሉ በሁሉም ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት የተሻለ የኢኮኖሚ እድገት ማስመዝገብ ተችሏል
ባሕር ዳር ፤ ሐምሌ 23/2018(ኢዜአ)፦በአማራ ክልል በሁሉም ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት የተሻለ የኢኮኖሚ እድገት ማስመዝገብ መቻሉን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ።
የአማራ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር፣ 5ተኛ ዓመት የስራ ዘመን 12ኛ መደበኛ ጉባኤ በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።
የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ፤ ለምክር ቤት ባቀረቡት የ2018 በጀት ዓመት የእቅድ አፈጻጸም ሪፖርት፤ በተለያየ መስክ በተቀናጀና በተናበበ መንገድ በመሰራቱ የተሻለ እድገት ማስመዝገብ አስችሏል ብለዋል።
በክልሉ በሁሉም ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት የተሻለ የኢኮኖሚያዊ እድገት ማስመዝገብ መቻሉን ገልጸው በተለይም በግብርና፣ በአገልግሎት፣ በኢንዱስትሪ፣ በማዕድን፣ በቱሪዝም እና ሌሎችም ዘርፎች እመርታዊ እድገት መታየቱን ገልጸዋል።
በዚህም የሰብል ምርታማነትን በሄክታር ከ28 ነጥብ 68 በመቶ ወደ 30 ነጥብ 46 በመቶ ማሳደግ መቻሉን ገልፀዋል።
በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄም በርካታ ኢንዱስትሪዎችን ወደ ማምረት በማስገባት ተኪ ምርቶችን ከማምረት ባለፈ ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን በማቅረብ የተሻለ አፈፃፀም ማስመዝገብ መቻሉን አንስተዋል።
በማዕድን ዘርፋም ለኮንስትራክሽንና ለኢንዱስትሪ ግብአት የሚሆኑ ምርቶችን ከማምረት ባሻገር ወርቅ፣ ኦፓልና መሰል ማዕድናትን ለገበያ በማቅረብ የውጭ ምንዛሬ ገቢ በማስገኘት አበረታች ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል።
በክልሉ የሚገኙ ታሪካዊና የተፈጥሮ የቱሪስት የመስህብ ስፍራዎችን በስፋት በማስተዋወቅ ከጎብኝዎች ከ15 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ማግኘት እንደተቻለም ጠቅሰዋል።
በበጀት ዓመቱ ከ1 ነጥብ 3 ሚሊዮን በላይ ዜጎች የስራ እድል በመፍጠር ተጠቃሚ እንዲሆኑ ተደርጓል ብለዋል።
በተጨማሪም የገበያ ዋጋ በማረጋጋትና የኑሮ ውድነትን በመከላከል በተሻለ ቅንጅት መሰራቱን አንስተው፤ በዚህም የተመዘገበው እድገት የበለጠ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
በአጠቃላይ በተከናወኑ ተግባራት የተመዘገቡ ውጤቶች የሚያበረታቱ ቢሆንም አሁንም ከዚህ በተሻለ ትብብር የክልሉን ህዝብ የላቀ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።