በደቡብ ጎንደር ዞን በሩዝ ሰብል ለማልማት ከታቀደው ውስጥ 91 በመቶውን ለማሳካት ተችሏል- መምሪያው - ኢዜአ አማርኛ
በደቡብ ጎንደር ዞን በሩዝ ሰብል ለማልማት ከታቀደው ውስጥ 91 በመቶውን ለማሳካት ተችሏል- መምሪያው
ጎንደር፤ ሐምሌ 22 /2018 (ኢዜአ) ፡-በደቡብ ጎንደር ዞን በያዝነው ክረምት በሩዝ ሰብል ለማልማት ከታቀደው 107 ሺህ ሄክታር መሬት ውስጥ 91 በመቶውን በዘር መሸፈን መቻሉን የዞኑ ግብርና መመሪያ አስታወቀ።
የመመሪያው ኃላፊ አቶ የሺጥላ አፍቃዴ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ የሩዝ ልማት ስራው አርሶ አደሩ በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናውን እንዲያረጋግጥ ከማድረግ ባሻገር ለገበያ የሚቀርብ ምርት እንዲኖረው አድርጓል።
በተያዘው ክረምትም በፎገራ ፣ ሊቦከምከምና ደራ ወረዳዎች 107 ሺህ ሄክታር መሬት በሩዝ ሰብል ለመሸፈን ታቅዶ እስከ አሁን በተደረገው ጥረት 91 በመቶውን ለማሳካት ተችሏል ነው ያሉት።
አርሶ አደሩ ቴክኖሎጂንና ግብአትን በአግባቡ በመጠቀም በሩዝ ልማት ስራው ምርታማነቱን እንዲያሳድግም የባለሙያዎች ድጋፍና ክትትል እየተደረገለት መሆኑን ተናግረዋል።
ይህም ባለፈው ዓመት የመኸር ወቅት በሄክታር በአማካይ የተገኝውን 56 ኩንታል የሩዝ ምርት በዘንድሮው ዓመትም ወደ 65 ኩንታል ለማሳደግ የተያዘውን ግብ ለማሳካት ያስችላል ብለዋል።
አሁን ላይ የሩዝ ልማት ከመስፋፋቱና ምርታማነቱ ከማደጉ ጋር ተያይዞ አርሶ አደሩ ከራሱ ፍጆታ አልፎ ለሀገር ውስጥ ገበያ የማቅረብ አቅም መገንባቱን አስረድተዋል።
ከአካባቢው የአየር ንብረት ሁኔታ ጋር የተቀናጀው የሩዝ አመራረት ሂደት፣ የምግብ ዋስትና በአስተማማኝ ሁኔታ ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት ከማገዝ ባለፈ አርሶ አደሩ ለገበያ የሚተርፍ ምርት እንዲያገኝ አድርጓል ብለዋል።
በወረታ ከተማ አስተዳደር የወረታ ዙሪያ ቀበሌ ነዋሪው አርሶ አደር አብራራው ጀግኔ፤ በሩዝ ልማት ስራ ምርታማነታቸውን በማሳደግ ሃብት ለመፍጠር እንደቻሉ ነው የሚናገሩት።
በዘንድሮው ዓመትም በአንድ ሔክታር መሬት ላይ የተሻሻሉ የሩዝ ዘርና ግብአት ተጠቅመው በመዝራት የተሻለ ምርት ለማግኝት እየሰሩ መሆኑን አመልክተዋል።
ሌላው የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ዳኛው አልጣህ በበኩላቸው፤የነበራቸው መሬት ውኃ የሚተኛበት በመሆኑ ከሚዘሩት ጤፍና ኑግ በቂ የሆነ ምርት ስለማይገኝ ለተረጂነት ተጋልጠው እንደቆዩ ነው የሚናገሩት።
ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን ተግባራዊ የተደረገው የሩዝ ልማት ስራ ውሃማ አካባቢን የሚፈልግ በመሆኑ ምርታማ በመሆን ሃብት ለመፍጠር መቻላቸውን ነው የገለጹት።
ገለባውንና ተረፈ ምርቱንም በመኖነት በመጠቀም ከብት በማደለብ እና በወተት ልማት በመሰማራት በተሻለ መንገድ ተጠቃሚ መሆናቸውን ነው የሚገልጹት።