ቀጥታ፡

የቡና ጥራትና ምርታማነትን ለማሻሻል የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ

እምድብር፤ ሐምሌ 18/2018(ኢዜአ):- የቡና ጥራትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ  የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን አስታወቀ፡፡

የባለስልጣኑ ሰራተኞች የቡና ችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር በጉራጌ ዞን በእምድብር ከተማ በሰሜ ቀበሌ አካሄደዋል ።


 

የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን የዋና ዳይሬክተር ፅህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ሰፊሳ አባቡ በወቅቱ እንደገለፁት የቡና ጥራትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው፡፡

ለዘርፉ በተሰጠው ልዩ ትኩረት የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን ተደራሽ በማድረግ ምርትና ምርታማነት ወደ ላቀ ደረጃ ማድረስ መቻሉን ተናግረዋል።


 

በዘርፉ በቅንጅት በተሰራው ስራ በቡና ምርታማነት ላይ የተገኘው ውጤት ተጠናክሮ እንዲቀጥል ይሰራል ብለዋል፡፡

የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ቡናና ቅመማቅመም ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ቶፊቅ ጁሃር የቡና ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ በተሰጠው ትኩረት ስኬት እየተመዘገበ ነው ብለዋል።

በዘንድሮ አመት በክልሉ 48 ሚሊዮን ችግኝ የመትከል ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡


 

በሽታ የሚቋቋሙ፣ በአጭር ጊዜ የሚደርሱና ምርታማ የሆኑ ዝርያቸው የተሻሻሉ የቡና ችግኞች ለአርሶ አደሩ እየቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በብልፅግና ፓርቲ የጉራጌ ዞን ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት የፖለቲካ ዘርፍ ሃላፊ አቶ ደሳለኝ ፈቀደ የቡና ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንዲቀጥሉ በቅንጅት ይሰራል ብለዋል።


 

ወጣቶች ቡና በስፋት እና በጥራት በማምረት  እንዲሁም በፍራፍሬ ልማት ላይ እንዲሳተፉ መደረጉን ያነሱት ደግሞ የእምድብር ከተማ ከንቲባ አቶ ግንባሩ በርጋ ናቸው ።

የከተማው ወጣት ዳዊት ትእዛዙ በ4 ሄክታር መሬት ላይ ዝርያቸው የተሻሻሉ የቡና ችግኞች እያለማ መሆኑን ተናግሮ ዘንድሮም ይህን በማስፋት ከ2 ሺህ በላይ ችግኝ  መትከሉን ተናግሯል፡፡

ሌላው በእምድብር ከተማ በቡና ልማት የተሰማሩት አቶ ሳሙኤል ፍራንሷ በበኩላቸው ባላቸው 3 ሄክታር ማሳ ላይ ቡና እያለሙ መሆኑን ጠቁመው ዘንድሮ ከ1 ሺህ በላይ የተሻሻለ የቡና ችግኝ መትከላቸውን ገልጸዋል፡፡
 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም