በከሚሴ ከተማ የተገነባው የኮሪደር ልማት ከተማዋን ከማስዋብ የንግድ እንቅስቃሴን አነቃቅቷል - ኢዜአ አማርኛ
በከሚሴ ከተማ የተገነባው የኮሪደር ልማት ከተማዋን ከማስዋብ የንግድ እንቅስቃሴን አነቃቅቷል
ደሴ፤ ሐምሌ 18/2018(ኢዜአ)፦ በከሚሴ ከተማ የተገነባው የኮሪደር ልማት ለከተማዋ ውበት ከመፍጠር ባሻገር የንግድ እንቅስቃሴ እንዲነቃቃ ማስቻሉን የከተማዋ ነዋሪዎች ገለፁ።
በከሚሴ ከተማ በንግድ ስራ የተሰማሩት አቶ አህመድ ጁሃር ለአዜአ እንደገለጹት፣ የተገነባው የኮሪደር ልማት ለከተማዋ ተጨማሪ ውበት ከመፍጠሩ ባሻገር፤ ለኢንቨስትመንት፣ ለንግድና ለነዋሪዎቿ የተመቸች እንድትሆን አድርጓል።
የኮሪደር ልማቱ ለረጅም ጊዜ ሲነሱ የነበሩ የሕዝብ ጥያቄዎች የመለሰ በመሆኑ ቀጣይነት ያለውና ውጤታማ እንዲሆን በገንዘባችንና በጉልበታችን ተሳትፎ እናደርጋለን ብለዋል።
በአሁኑ ወቅት በተለያየ መስክ የተጀመሩ የልማት ስራዎች ቀጣይ እንዲሆኑም ከመንግስት ጎን ተሰልፈን ሰላማችንን በመጠበቅ የዜግነት ግዴታችን እንወጣለን ነው ያሉት።
ሌላዋ የከተማዋ ነዋሪ ወይዘሮ ጣይቱ አሰፋ በበኩላቸው በከተማዋ ስንፈልገው የነበረ ልማት ተግባራዊ በመደረጉ ተጠቃሚ ሆነናል ሲሉ ገልጸዋል።
የኮሪደር ልማቱ በተለይ የቆሻሻ መጣያ የነበሩና ለአይን የማይማርኩ ስፍራዎችን በማስዋብ ለእንቅስቃሴና ለመዝናኛ ምቹ ማድረግ በመቻሉ የከተማዋ ገጽታ መቀየሩን ተናግረዋል።
የከሚሴ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሸሪፍ ቃሲም በበኩላቸው፣ የከተማውን ሰላም ከማስጠበቅ ጎን ለጎን ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ በርካታ ልማቶች እየተከናወኑ ነው ብለዋል።
በልማቱ የተሽከርካሪ፣ የብስክሌትና የእግረኛ መንገድ ተለይቶ ከመሰራቱ ባለፈ የአረንጓዴ ሥፍራዎችና የህዝብ መዝናኛዎችን አካቶ መገንባቱን ነው የገለጹት።