ቀጥታ፡

በሲዳማ ክልል በበልግ እርሻ ምርታማነትን የሚያሳድጉ ተግባራት ተከናውነዋል - ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ

ሀዋሳ፤ ሐምሌ 17/2018(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል በበልግ ወቅት እርሻ ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ ተግባራት መከናወናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ፡፡

ርዕሰ መስተዳደሩን ጨምሮ የክልል፣ የዞንና የወረዳ አመራሮች በሀዋሳ ዙሪያ፣ በደራራ፣ በብላቴ ዙሪያ እና በዳሌ ወረዳዎች በበልግ የለማ ማሳ የመስክ ምልከታ አድርገዋል።

ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ በወቅቱ እንዳሉት በልግ አብቃይ በሆኑ አካባቢዎች በበቆሎ፣ ቦሎቄና ሌሎች ሰብሎች የለማው ማሳ በመልካም ሁኔታ ላይ ይገኛል።


 

በምርት ወቅቱ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ለግብአት አጠቃቀምና ለግብርና ቴክኖሎጂ ትኩረት ተሰጥቶ መከናወኑን ጠቁመዋል።

በበልግ እርሻው ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት በመኽር ወቅትም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል።


 

የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ሀላፊ ታምሩ ሞኬ በበኩላቸው በክልሉ በበልግ እርሻ 152 ሺህ ሄክታር ማሳ በበቆሎ፣ ቦሎቄና ስራ ስር ሰብሎች መልማቱን ተናግረዋል።

ከዚህ ውስጥ 67 ሺህ ሄክታር የሚሆነው በበቆሎ መልማቱን ጠቁመው በምርት የተሸፈነውን ማሳ ውጤታማ ለማድረግም የእንክብካቤና የክትትል ስራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን አመልክተዋል፡፡


 

የሀዋሳ ዙሪያ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር አለማየሁ ዲጋ በበኩላቸው አንድ ሄክታር ማሳ ላይ ያለሙት በቆሎ በመልካም ቁመና ላይ መሆኑን ተናግረዋል።

ከግብርና ባለሙያ በሚሰጣቸው ምክር በመታገዝ እርጥበትን በማሳ ውስጥ እንዲቆይ በማድረጋቸው የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ አመላክተዋል።


 

አርሶ አደር ጸሀይ በቀለ በበኩላቸው በማሳቸው ውስጥ እርጥበትን የማቆየት ስራ በመስራታቸው የበቆሎ ሰብላቸው በመልካም ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም