ቀጥታ፡

በክልሉ የግብር አከፋፈል ስርአቱን ቀልጣፋና አስተማማኝ ለማድረግ እየተሰራ ነው

ባህርዳር፤ሐምሌ 17/2018 (ኢዜአ)፦ የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ የግብር አከፋፈል ስርአቱን በቴሌ ብር በማድረግ ቀልጣፋና አስተማማኝ ስርአት ለመዘርጋት እየሰራ መሆኑን አስታወቀ።

የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ የግብር አከፋፈል ስርአቱን በቴሌ ብር ለማድረግ የሚያስችል ስምምነት ኢትዮ ቴሌኮም ጋር ዛሬ ማምሻውን ተፈራርሟል።

የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ ሃላፊ መንገሻ ፈንታው (ዶ /ር) በወቅቱ እንደገለጹት፥ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ90 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ በመሰብሰብ በራስ አቅም የመልማት ባህልን በማጎልበት አበረታች ውጤት ተገኝቷል።

በአዲሱ በጀት ዓመትም የግብር ስርአቱን ዲጅታላይዝ በማድረግ ግልጽ፣ ቀልጣፋና ተአማኒነት ያለው የግብር ስርአት ለመገንባት ከባህርዳር ዩኒቨርሲቲና ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በትብብር እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር የተደረሰው ስምምነትም ወደ ኢ-ታክስ ሲስተም የገቡ 420 ሺህ የደረጃ “ለ” ግብር ከፋዮችን ጨምሮ የደረጃ "ሀ" እና "ሐ" ግብር ከፋዮች ግብራቸውን በቀላሉና በፍጥነት ባሉበት ቦታ ሆነው እንዲከፍሉ የሚያስችል መሆኑን አመልክተዋል።

በተጨማሪም የግብር ስርአቱን ተደራሽ ለማድረግና በዘርፉ የሚስተዋለውን ብልሹ አሰራር ለማስቀረት የሚያስችል መሆኑንም ጠቁመዋል።

በኢትዮ ቴሌኮም ችፍ የሞባይል ባንኪንግ ቢዝነስ ኦፊሰር አቶ ቡሩክ አዳነ በበኩላቸው፥ ከክልሉ ገቢዎች ቢሮ ጋር የተደረገው ስምምነት ዲጅታል 2030ን እውን ለማድረግ የሚያስችል ነው ብለዋል።

ቢሮው ባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ ያበለጸገውን የኢ-ታክስ ሲስተም ከቴሌ ብር ጋር በማስተሳሰር ደንበኞች በቀላሉ ግብራቸውን የሚከፍሉበት ስርአት ለመገንባት የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል።

የግብር ክፍያውን በቴሌ ብር ለማድረግም በዩኒቨርሲቲው የበለጸገውን ሲስተም ከቴሌብር ጋር እንዲናበብ በማድረግ፣አሰራሩን በመፈተሽና የደህንነት ጉዳዮችን የማረጋገጥ ስራ ቀድሞ ማጠናቀቁን ተናግረዋል።

ደንበኞችም ከገቢዎች ቢሮ የሚሰጠውን የመክፈያ ኮድ በማስገባት ግብራቸውን በቴሌብር በቀላሉ፣ በፍጥነትና አስተማማኝነት ባለው መንገድ እንዲከፍሉ የሚያስችል ነው ብለዋል።

አያይዘውም ኩባንያው ቴሌብር የሚጠቀሙ ደንበኞችን ቁጥር 60 ነጥብ 5 ሚሊየን ማድረሱን ጠቁመው ባለፉት አምስት ዓመታትም 9 ትሪሊዮን የሚጠጋ የገንዘብ ዝውውር ማድረግ መቻሉን አውስተዋል።

የባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት መንገሻ አየነ በበኩላቸው፥ ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር፣ ምርምር፣ ማህብረሰብ አገልግሎትና ቴክኖሎጂ ሽግግር ባሻገር ከተቋማት ጋር በቅንጅት ለሀገር እድገት የሚበጁ ተግባራትን አያከናወነ ይገኛል ብለዋል።

ከክልሉ ገቢዎች ቢሮ ጋር በመተባበርም የኢ-ታክስ ፕሮጀክትን በማልማት የዘርፉን ችግር ለመፍታት መስራቱን ጠቁመው፥ አሁን ላይ ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር የተደረሰው ስምምነት የኢ-ታክስ ሲስተሙን ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችል ነው ሲሉ አክለዋል።

ማምሻውን በተካሄደው ስምምነት ላይም የቢሮው የማኔጅመንት አበላት፣ የኢትዮ-ቴሌኮም የስራ ሃላፊዎች፣ የባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ አመራሮች ተገኝተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም