ቀጥታ፡

በክልሉ በኢኮኖሚና በማህበራዊ ዘርፍ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ተግባራት ተከናውነዋል - ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ

አርባ ምንጭ፤ ሐምሌ 17/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በኢኮኖሚና በማህበራዊ ዘርፎች ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ተግባራት መከናወናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ተናገሩ፡፡

ርዕሰ መስተዳድሩ እየተካሄደ ባለው የክልሉ ምክር ቤት መደበኛ ጉባኤ ላይ ባቀረቡት ሪፖርት እንዳመለከቱት፤  በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በኢኮኖሚና በማህበራዊ ዘርፍ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ተግባራት ተከናውነዋል፡፡

ከዚህ ውስጥም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ300 ሺህ በላይ ዜጎች በገጠርና በከተማ የስራ ዕድል ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል።

የስራ ዕድል ለተፈጠረላቸው ዜጎችም የመስሪያ እና የመሸጫ ቦታ፣ የመነሻ ካፒታል፣ የገበያ ትስሰር እና የድጋፍና ክትትል ስራዎች መከናወናቸውን ነው የጠቀሱት፡፡


 

በቱሪዝም ዘርፉም ልዩ ትኩረት በመሰጠቱ ዘርፉ እየተነቃቃ መምጣቱን ጠቅሰው ክልሉን ከጎበኙ የሀገር ውስጥና የውጭ ጎብኚዎች ከ1 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን ገልጸዋል።

በበጀት አመቱ በክልሉ ያለውን የገቢ አማራጮች አሟጦ ለመሰብሰብ በተከናወነው ተግባር 32 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ ተችሏል ነው ያሉት።

ከተሞችን ከማልማት አኳያም ለኑሮ ምቹ እና ጽዱ ለማድረግ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑንና ከዚህም በ27 ከተሞች እየተገነባ ያለው የኮሪደር ልማት ስራን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡

በሌላ በኩል በማህበራዊ ዘርፍም የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ተግባራት መከናወናቸውን አንስተው በትምህርትና በጤና የተከናወኑ ውጤታማ ተግባራትን ጠቅሰዋል፡፡

በዚህም በትምህርት ለትውልድ ንቅናቄ ከ768 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት ሀብት በመሰብሰብ የትምህር ቤቶችን ደረጃ የማሻሻል፣ ግብዓቶችን የማሟላት፣ የመምህራንን አቅም የመገንባትና ሌሎች ስራዎች መከናወናቸውን አመላክተዋል፡፡


 

በጤናው ዘርፍ የመሰረተ ልማት ግንባታና እና ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት የህብረተሰቡን እርካታ ማረጋገጥ ያስቻሉ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል፡፡

የጤና አገልግሎት ፍትሐዊነትን ለማረጋገጥ ጉልህ ሚና ያለው የማህበረሰብ ጤና መድህን አባላት ቁጥር እየጨመረ የመጣ ሲሆን ከአንድ ሚሊየን በላይ አባላትን ማፍራት መቻሉን ጠቅሰዋል፡፡

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 7ኛ መደበኛ ጉባኤውን እያካሄደ የሚገኝ ሲሆን ምክር ቤት አባላት ርዕሰ መስተዳድሩ ባቀረቧቸው ሪፖርት ዙሪያ ውይይት በማድረግ ላይ ይገኛሉ።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም