የበና ፀማይ ወረዳ አርብቶ አደሮች በመስኖ ልማት ስራ ላይ በመሳተፍ ተጠቃሚ እየሆኑ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የበና ፀማይ ወረዳ አርብቶ አደሮች በመስኖ ልማት ስራ ላይ በመሳተፍ ተጠቃሚ እየሆኑ ነው
ጂንካ፤ ሐምሌ 15/2018(ኢዜአ) :- በደቡብ ኦሞ ዞን በና ፀማይ ወረዳ በመስኖ ልማት ስራ ላይ በስፋት በመሳተፍ ተጠቃሚ መሆናቸውን የአካባቢው አርብቶ አደሮች ተናገሩ።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የሚገኘው የደቡብ ኦሞ ዞን በቆላማነት ከሚጠቀሱ አከባቢዎች አንዱ በመሆኑ በተለይም የመስኖ ልማት ስራ ልዩ ትኩረት የተሰጠበት ስፍራ ሆኗል።
በዚሁ መሰረትም አርሶና አርብቶ አደሮች የአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም የተለያዩ የግብርና ምርቶችን በስፋት በመስኖ ማምረታቸውን አጠናክረው ቀጥለዋል።
በዞኑ በና ፀማይ ወረዳ ከሚገኙት መካከል ኢዜአ ያነጋገራቸው አርብቶ አደሮች የመስኖ ልማት ስራ በስፋት በማከናወን ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል።
በወረዳው የጊስማ ባቦ ቀበሌ ነዋሪ ባካ ዋልታ፤ አከባቢው የዝናብ እጥረት ያለበት መሆኑን ታሳቢ በማድረግ በመንግሥት የተገነባው የመስኖ አውታር የእርሻ ስራው እንዲስፋፋ አድርጓል ብለዋል ።
ከመስኖ ልማት በተጨማሪ በእንስሳት እርባታና ተያያዥ የግብርና ልማት ስራዎች ለራሳቸውና ለቤተሰባቸው በምግብ ራስን ለመቻል መብቃታቸውን ተናግረዋል።
በወረዳው የዱማ ቀበሌ የሚኖረው ወጣት ሻዳ አይኬ በበኩሉ፤ በመንግሥት በተዘረጋው የመስኖ አውታር ተጠቅሞ ዘንድሮ በ1 ነጥብ 5 ሄክታር መሬት ላይ የተከለው ሽንኩርት ከፍተኛ ገቢ የሚጠብቅ መሆኑን ገልጿል።
የመስኖ ልማትን በአግባቡ መጠቀም ከጀመረ ወዲህ በእርሱና ቤተሰቡ ላይ ለውጥና መሻሻል መኖሩን አንስቶ ስራውን አጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን ተናግሯል።
በበና ፀማይ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት የግብርና ቴክኖሎጂ ኤክስቴንሽን ባለሙያ አንተነህ መኮንን፤ በወረዳው የአርብቶ አደሮችን የኑሮ ዘይቤ በማሻሻል የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ጥረቶች ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆኑን ተናግረዋል።
ከጂንካ ግብርና ምርምርና ከሌሎች ተቋማት ጋር በመቀናጀት 'ዊሊያም'' እና ''አምቦሀ'' በተባለው የተሻሻለ የሙዝ ዝርያን ጨምሮ የተሻሻሉ የሰብል፣ የሆርቲካልቸር ዝርያዎችን በማላመድ ለአርብቶ አደሩ የማሰራጨት ስራ እየተሰራ ይገኛልም ነው ያሉት።
የደቡብ ኦሞ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ ምንላርገው አዲሱ፤ በዞኑ ''ከተረጂነት ወደ ምርታማነት'' የሚለውን መርህ ተግባራዊ በማድረግ ምርታማነትን የማስፋትና የማሳደግ ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል።
የአርብቶ አደሩን የመስኖ ልማት አጠቃቀም በማሳደግ፣ አዳዲስ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በማስፋት እና የሜካናይዜሽን እርሻን በማስፋፋት የአርብቶ አደሮችን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።