በባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ከ55 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል ተፈጥሯል - ኢዜአ አማርኛ
በባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ከ55 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል ተፈጥሯል
ባህር ዳር ፤ሐምሌ 15/2018( ኢዜአ)፡-በባህር ዳር ከተማ አስተዳደር በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ55 ሺህ በላይ ለሆኑ ዜጎች የስራ እድል መፍጠር መቻሉን የከተማ አስተዳደሩ ስራና ክህሎት መምሪያ አስታወቀ።
የመምሪያው ኃላፊ አቶ ዘመነ አሰፋ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በተጠናቀቀው በጀት አመት ለ45 ሺህ 300 ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር ታቅዶ ከአቅድ በላይ ከ55 ሺህ የሚሆኑ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል።
የስራ እድል ከተፈጠረላቸው ዜጎች ውሰጥም ከ38 ሺህ በላይ ለሚሆኑት ቋሚ፣ቀሪዎቹ ደግሞ ጊዜያዊ የስራ እድል ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቅሰዋል።
የስራ እድሉ በውጭ ሀገር የስራ ስምሪት፣ በከተማ ግብርና፣ ማኑፋክቸሪንግ ፣ ኮንስትራክሽን፣ በአገልግሎትና ሌሎች ዘርፎች የተፈጠረ መሆኑን ተናገረዋል።
በዚህ ወቅት ሦስት ሺህ 65 የሚደርሱ ኢንተርፕራይዞችን በማደራጀት ወደ ስራ ማስገባት የተቻለ መሆኑንም ነው ያስረዱት።
ለስራ እድል ተጠቃሚዎች ከ321 ሚሊዮን ብር በላይ የሚሆን መደበኛና ተዘዋዋሪ ብድር ማመቻቸት እንደተቻለም ነው የጠቀሱት።
በተጨማሪም በ128 ሚሊዮን ብር ወጭ የስራ እድሉ ለተፈጠረላቸው ዜጎች የመስሪያ ማሽኖችን ማቅረብ መቻሉን ጠቁመው 125 ሼዶችና ኮንቴነሮችንም ማስተላለፍ መቻሉን አስገንዝበዋል።
የስራ እድል ከተፈጠረላቸው መካከል ወይዘሮ እናንዬ ታምሩ እንደገለጹት፤ ከ40 በላይ ሴቶች በአንድ ላይ ተደራጅተን አሳ የማቅረብ ፣የማዘጋጀትና የማከፋፈል ስራ በመስራት ውጤታማ ሆነናል።
የማህበሩ አባላትም ከሚያገኙት ገቢ ከእለት ፍጆታ ባለፈ የቁጠባ ባሕላቸውን ለማዳበር ያስቻላቸው በመሆኑም በዘርፉ በስፋት ወደ ስራ ለመግባት ጥረት እያደረጉ መሆኑን ነው የገለጹት።
ሁለት ሆነው በመደራጀት በጀመሩት የልብስ ስፌት ስራ ውጤታማ በመሆኑ ተጨማሪ ማሽኖችን በመግዛት ለሌሎች ስራ ለመፍጠር ጥረት እያደረጉ መሆኑን የተናገረችው ደግሞ ወጣት እናኑ ደሴ ናት።
አሁን ላይ በገቢም ሆነ በማምረት የተሻለ ቁመና ላይ እንገኛለን፤ለዚህም በከተማ አስተዳደሩ የተደረገልን ብድርና ሌሎች ድጋፎች ትልቁን ድርሻ ይወስዳል ብላለች።