ቀጥታ፡

በዞኑ ከ900 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በመኸር አዝመራ እየለማ ነው

አምቦ፤ ሐምሌ 14/2018 (ኢዜአ) ፡-በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ከ900 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በመኸር አዝመራ እየለማ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቀ፡፡

በዞኑ ኢልፈታ ወረዳ በመኸር አዝመራ በኩታ ገጠም 1 ሺህ 300 ሄክታር መሬት ላይ የቢራ ገብስ ዘር የመዝራት መርሃ ግብር የዞኑና የወረዳው የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት ተካሂዷል፡፡

የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ መርጋ አየለ እንደገለጹት፤ በመኸር እርሻው ከ900 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር የመሸፈን ሥራ እየተከናወነ ይገኛል፡፡


 

በመኸር አዝመራው በቆሎ፣ ገብስ፣ ማሽላ እና ስንዴ በኩታ ገጠም የሚለሙ ሲሆን፤ ከዚህ ውስጥ ከ48 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቢራ ገብስ ለማልማት ታቅዶ እስካሁን 22 ሺህ ሄክታር የሚሆነው በዘር መሸፈኑን ተናግረዋል።

በምርት ዘመኑ የተሻለ ምርት ለማግኘት በአሲድ የተጠቃን መሬት በኖራ በማከም፣ እንዲሁም ምርጥ ዘርና የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሮች በስፋት እየቀረበ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

የኢልፈታ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ፈይሳ ቶለሳ በበኩላቸው፤ የወረዳው አርሶ አደሮች የኩታ ገጠም አስተራረስ ዘዴን እየተላመዱ መምጣታቸውን ገልጸዋል፡፡


 

በዚህም ምርትና ምርታማነት እያደገ መምጣቱን ጠቁመው፤ በዘንድሮው የመኸር እርሻ በወረዳው 32 ሺህ 932 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለማልማት ታቅዶ እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል። 

ከዚህ ውስጥ 2 ሺህ 960 ሄክታር መሬት በቢራ ገብስ ለማልማት የታቀደ ሲሆን፣ እስካሁን በተከናወኑ ሥራዎች 83 በመቶ የሚሆነው በዘር መሸፈኑን አስረድተዋል።

የወረዳው አርሶ አደሮች በበኩላቸው፣ በግብርና ጽሕፈት ቤቱ በተደረገላቸው ድጋፍ የቢራ ገብስን በኩታ ገጠም ማልማት ከጀመሩ ወዲህ ገቢያቸው ማደጉን በመግለጽ ምርታቸውን ለማሳደግም ጥረት እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል።

አርሶ አደር ለሊሳ ገላና፤ ገብስን ቀደም ሲል በኩታ ገጠም ማረስ ሳይጀምሩ ከአንድ ሄክታር 15 ኩንታል ምርት ብቻ ያገኙ እንደነበር አብራርተው፣ አሁን ላይ የግብርና ባለሙያዎች የሚያደርጉላቸውን ድጋፍ ተጠቅመው ከአንድ ሄክታር እስከ 50 ኩንታል ምርት ለማግኘት እየሠሩ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ሌላው አርሶ አደር ኢትሳ ጃለታ፤ ገብስን በኩታ ገጠም ማረስ ከጀመሩ ሶስት ዓመት እንደሆናቸው ጠቅሰው፣ ምርጥ ዘርና የአፈር ማዳበሪያ በወቅቱ ስለሚያገኙ ምርታቸው እያደገ መምጣቱንና ዘንድሮም ከልማቱ ተጠቃሚ ለመሆን መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም