ቀጥታ፡

በጅማ ዞን የሩዝ ምርታማነት እያደገ መጥቷል

ጅማ፤ ሐምሌ 14/2018(ኢዜአ)፦ በጅማ ዞን የሩዝ ሰብልን ለማስፋፋት በተከናወነው ሥራ ምርታማነቱ እያደገ መምጣቱን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገልጿል።

በዞኑ በ2018/19 የምርት ዘመን 393 ሺህ 600 ሄክታር መሬት በሩዝ ሰብል ለመሸፈን ታቅዶ እስካሁን ከ370 ሺህ ሄክታር በላይ የመሬት ዝግጅት መደረጉን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ሚፍታህ ጋሊ ተናግረዋል።

በዞኑ 19 ወረዳዎች ሩዝ የሚለማ መሆኑን የገለጹት አቶ ሚፍታህ ባለፈው የምርት ዘመን ከ14 ሚሊዮን 800 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን ተናግረዋል።

ከዚህ በተጨማሪም ምርታማነቱን ለማስፋፋት ምርጥ ዘር የማባዛት ሥራ እየተከናወነ ሲሆን በዞኑ በሚገኙ የኅብረት ሥራ ዩኒየኖች አማካይነት ስኬታማ ሥራ መከናወኑን ተናግረዋል።

በዘንድሮ ዓመት በጅማ ዞን ቀርሳ ወረዳ የኅብረት ሥራ ዩኒየን በኩል 50 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ምርጥ ዘር ተባዝቶ በቴክኖሎጂ በመታገዝ ያለ ብክነት ተሰብስቧል ነው ያሉት።

ይህም ከውጭ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገባውን የሩዝ ሰብል ምርጥ ዘር በሀገር ውስጥ ለማምረት ታቅዶ እየተሠራ በመሆኑ ነው ብለዋል።


 

ከዚህ በተጨማሪም በሩዝ ሰብል ልማት ላይ ለበርካቶች የሥራ ዕድል ተፈጥሮ ተጠቃሚ እየሆኑ ነው ብለዋል።

በጅማ ዞን ቀርሳ ወረዳ በኅብረት ሥራ ዩኒየን በዘር ማባዛት ሥራ ላይ ተሰማርተው ባገኙት የሥራ ዕድል ውጤታማ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ ሲራጅ ጀማል እና ዛኪር አባራያ ናቸው።

ዞኑ ምቹ የአየር ጠባይ ያለው እንደመሆኑ በየጊዜው የተሻለ ምርት እየተሰበሰበ መሆኑን ተናግረዋል።

በዚህ ሥራ ላይ ከተሰማሩ በኋላ ሕይወታቸው እየተሻሻለ መሆኑን ገልጸው ከዚህ በተጨማሪም ባላቸው መሬት ላይ በማምረት ተጠቃሚ መሆናቸውን አክለዋል።

ወጣት ከድር አባዝናብ፤ ዩኒየኑ የሩዝ ሰብል ምርጥ ዘርን ለማስፋፋት እያከናወነ በሚገኘው የግብርና ሥራ ተሰማርቶ ከራሱ አልፎ ቤተሰቡን እያገዘ መሆኑን ጠቅሷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም