በክልሉ የመንግስት አገልግሎቶችን በቴክኖሎጂ የታገዘ በማድረግ ውጤታማ ስራ እየተሰራ ነው - ኢዜአ አማርኛ
በክልሉ የመንግስት አገልግሎቶችን በቴክኖሎጂ የታገዘ በማድረግ ውጤታማ ስራ እየተሰራ ነው
ባህር ዳር፤ሐምሌ 13/2018(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የመንግስት አገልግሎቶችን በቴክኖሎጂ የታገዙ በማድረግ ስኬታማ ስራዎች ማከናወን መቻሉን የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ገለፀ።
የቢሮው ምክትል ሃላፊ አቶ የቻለ ይግዛው በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የነበረውን ስራ አፈፃፀም አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ ፤ የመንግስት አሰራሮችን በቴክኖሎጂ በማዘመን የላቀ አገልግሎት ለመስጠት ተችሏል።
በተለይም ከለውጡ ዓመታት ወዲህ ቴክኖሎጂን በማዘመን በኩል የተሰጠው ልዩ ትኩረት ዘርፉ በፍጥነት እንዲያድግና ውጤታማ እንዲሆን ማስቻሉን ተናግረዋል።
ለዚህም የቴክኖሎጂ የእውቀት ክፍተትን በስልጠና ለመሙላት፣ የፈጠራ አቅምን ለማሳደግ እና በዘርፉ በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ ሆኖ ለመዝለቅ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መሰጠቱን ገልፀዋል።
በክልሉ ከ725 ሺህ በላይ ወገኖችን ለማሰልጠን ታቅዶ ወደ ስራ የተገባ ሲሆን በሁለት ዙር ከ1 ነጥብ 3 ሚሊዮን በላይ ወገኖችን ስልጠናውን መውሰዳቸውን ተናግረዋል።
በዘርፉ ስኬታማ ስራዎችን ለማከናወን የተቻለው በየደረጃው የሚገኘው አመራር በልዩ ቁርጠኝነት ስራዎችን ለማከናወን በመቻሉ ነው ብለዋል።
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ6 ነጥብ 8 ሚሊዮን በላይ ወገኖችን የፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ ባለቤት ማድረግ እንደተቻለ አመልክተዋል።
በአዲሱ በጀት ዓመትም በገጠርና በከተማ 12 ሚሊዮን ለሚደርሱ ዜጎች የዲጅታል መታወቂያን ተደራሽ ለማድረግ ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል።
ከዚህ ባለፈም የተቋማትን አገልግሎትን ፈጣን፣ ቀልጣፋና ከእጅ ንክኪ የራቀ ለማድረግም በዋና ዋና ከተሞች የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት መጀመሩን ጠቅሰዋል።
በዚህም በክልል ደረጃም በባህር ዳር፣ ደሴና ወልዲያ ከተሞች አገልግሎቱን በማስጀመር የህዝብ ቅሬታዎችን መፍታት መቻሉን ገልፀዋል።
በክልል ደረጃ በተቋቋመው መሶብ የአንድ ማዕከል ቀደም ሲል ተደጋጋሚ ቅሬታ ይቀርብባቸው የነበሩ በ15 ተቋማት 65 አገልግሎቶችን መስጠት መቻሉን አስገንዝበዋል።
በቀጣይም በጎንደር፣ ደብረ ታቦር ፣ ደብር ብርሃንና ኮምቦልቻ ከተሞች አገልግሎቱን ለማስፋት የግንባታና ሌሎች ቅድመ ዝግጅት ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን አብራርተዋል።
ቴክኖሎጂን ማስፋፋት የህዝብን እንግልትና ድካም የሚቀንሱ አሰራሮችን ይበልጥ በማሳደግ የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አንስተው፤ ለውጤታማነቱ ሁሉም በላቀ ቅንጅት መስራት እንዳለበት አሳስበዋል።