ቀጥታ፡

የሕዳሴ ግድብ የዘመናት ኢ-ፍትሐዊነትን የሻረ የጋራ ተጠቃሚነት ተምሳሌት ነው

አዲስ አበባ፤ሐምሌ 13/2018 (ኢዜአ)፦ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በዓባይ ወንዝ ላይ ነበረውን የዘመናት ኢ-ፍትሐዊ የውሃ ሃብት አጠቃቀም ያስወገደ፣ አዲስ የትብብር እና የጋራ ተጠቃሚነት ተምሳሌት መሆኑን የሕዝብ ተወካች ምክር ቤት አባል መሐመድ አል-አሩሲ ገለጹ፡፡

ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ኢትዮጵያውያን የታሪክ ቁጭታቸውን በተግባር ለመቀየር የቆረጡበትና በማንኛውም ውጫዊ አካል ሳይሆን በራሳቸው የውስጥ አቅምና በሕዝብ ሁለንተናዊ አስተዋጽኦ ብቻ የተገነባ ታሪካዊ ፕሮጀክት ነው።

ይህ ግዙፍ ፕሮጀክት አገሪቱ ካላት የተፈጥሮ ሀብት ተጠቃሚ ለመሆን የምታደርገውን ጥረት የሚያሳይ ከመሆኑም በላይ፣ በታዳሽ ኃይል ልማት ረገድ የኢኮኖሚና የቴክኖሎጂ ሉዓላዊነቷን ለማረጋገጥ የጀመረችውን ስልታዊ ጉዞ በግልጽ ያሳያል።

ይህ የኢትዮጵያውያን የመቻል አቅም ማረጋገጫ የሆነው ሜጋ ፕሮጀክት፣ የአፍሪካ አገራት የራሳቸውን የውስጥ አቅም አስተባብረው ከተንቀሳቀሱ ያለምንም ውጭ ድጋፍ ትልልቅ የልማት ግቦችን ማሳካት እንደሚችሉ ትልቅ ማሳያ ሆኗል።

በመሆኑም ግድቡ ለአፍሪካ አህጉር ነፃነትና ራስን የመቻል አዲስ ተስፋን በማስረፅ ረገድ ታላቅ ኩራትና የማይደበዝዝ የታሪክ ትምህርት የሰጠ ሆኖ ተመዝግቧል።

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል መሐመድ አል-አሩሲ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ግብፅ በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ የምታነሳቸው ነጥቦች ታሪካዊ እውነታዎችን፣ የላይኛው ተፋሰስ አገራትን የልማት መብት እንዲሁም ዓለም አቀፍ የውሃ አስተዳደር ሕጎችን የሚጋፉ መሆናቸውን አስረድተዋል።

ይህ የግብፅ አካሄድ ጊዜ ያለፈበትን የውሃ የበላይነት ዘመን እንደገና ለማንፀባረቅ የሚደረግ ዋጋ ቢስ ሙከራ መሆኑንም ጠቁመዋል።

ኢትዮጵያ የምታከናውናቸው ተግባራት በሙሉ ዓለም አቀፋዊ መርሆዎችን የተከተሉ መሆናቸውን የምክር ቤት አባሉ አብራርተዋል።

ዓለም አቀፍ ሕግ የላይኛው ተፋሰስ አገራትን ያገለለ እና በቅኝ ግዛት ዘመን የተፈረሙ ስምምነቶችን እንደማይቀበል የገለጹት አቶ መሐመድ፣ ኢትዮጵያ፣ ግብፅ እና ሱዳን በ2015 ዓ.ም በካርቱም የፈረሙትን የመርሆች መግለጫ በማስታወስ ግድቡን የመሙላት ሂደት ከዚህ ስምምነት ጋር በሚጣጣም መልኩ መከናወኑን አስረድተዋል።

ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ የገነባችው ታላቁ የህዳሴ ግድብ የቀደመውን ኢ-ፍትሃዊ አሰራር በመቀየር፣ መላውን የናይል ተፋሰስ ይበልጥ ፍትሃዊ፣ ምክንያታዊ እና ሁሉን አቀፍ በሆነ መንገድ ለመምራት የሚያስችል ታሪካዊ ሽግግር መፍጠሩንም ገልጸዋል።

የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሙሉ በሙሉ በኢትዮጵያውያን የውስጥ አቅምና ሀብት የተከናወነ መሆኑን ነው ያስታወሱት

መሐመድ አል-አሩሲ፣ ፕሮጀክቱ የሕዝቡን የልማትና የእድገት ፍላጎት በግልጽ የሚያሳይ የታሪክ አሻራ መሆኑን አስታውቀዋል።

በዚህም ኢትዮጵያ ግድብ መገንባት ብቻ ሳይሆን፣ በናይል ተፋሰስ ቀጠና ውስጥ አዲስ የፍትህ እና የእኩልነት ታሪክ ጽፋለች ብለዋል።

ግብፅ የድርድር ሂደቱን በተደጋጋሚ በማዘግየትና ከግድቡ ቴክኒካዊ ወሰን ውጭ የሆኑ ሰፊ የውሃ ክፍፍል አጀንዳዎችን በማንሳት የፕሮጀክቱን ጉዞ ለማደናቀፍ ስትሞክር መቆየቷን የፓርላማ አባሉ አስታውሰዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም