ቀጥታ፡

የመሶብ ዲጂታል የአንድ ማዕከል አገልግሎት የሕዝብና መንግሥትን መተማመን እያጎለበተ ነው 

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦የመሶብ ዲጂታል የአንድ ማዕከል አገልግሎት በመንግስት እና በህዝብ መካከል ያለው መተማመን እንዲጎለብት ማድረጉን የአዲስ መሶብ ዲጂታል የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር ደሳለኝ ተረፈ ገለጹ።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባለፉት ሶስት ተከታታይ ቀናት ሲያካሂድ የነበረውን የ2018 በጀት ዓመት እና የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ አፈፃጸም ግምገማ በስኬት አጠናቋል። 

በዚሁ መድረክ ላይ ከተማ አስተዳደሩ በበጀት ዓመቱ በጥቅሉ ከ96 በመቶ በላይ የሚሆን የአፈፃጸም ስኬት ማስመዝገብ እንደቻለ ተገልጿል።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በወቅቱ ባደረጉት ንግግር፤ መድረኩ በበጀት ዓመቱ ለመፈጸም የተቀመጡ ታላላቅ ግቦች እንዲሁም ባለፉት አምስት ዓመታት የተከናወኑ ስትራቴጂክ ዕቅዶች ምን ያህል ውጤታማ በሆነ መንገድ እንደተከናወኑ በጥልቀት የተገመገመበት መሆኑን ገልጸዋል።

የአዲስ መሶብ ዲጂታል የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር ደሳለኝ ተረፈ፤ ቀደም ሲል ከፍተኛ ስብራት የነበረበትን የአገልግሎት ዘርፍ ለማሻሻል እና የህዝቡን እርካታ ለማረጋገጥ ባለፉት አምስት ዓመታት በርካታ ስራዎች ሲሰሩ መቆየታቸውን ገልጸዋል።

የአገልግሎት አሰጣጥን ይበልጥ ዘመናዊ፣ ቀልጣፋና ተደራሽ ለማድረግ ታስቦ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ይፋ የተደረገው የመሶብ ዲጂታል የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ከተማ አስተዳደሩ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራበት እንደሚገኝ ተናግረዋል።

በአራዳ ክፍለ ከተማ የተጀመረው ዘመናዊው የአዲስ መሶብ ዲጂታል አገልግሎት በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ 11 ቋሚ ቦታዎች እና አንድ ተንቀሳቃሽ ማዕከል ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል።

በአሁኑ ወቅት የ 25 ተቋማትን 150 የተለያዩ አገልግሎቶች በአንድ ጣራ ስር በማስተናገድ ላይ የሚገኘው ይህ ስኬታማ የዲጂታል ሽግግር ፕሮጀክት፣ በቀጣይም ተደራሽነቱን ይበልጥ ለማስፋፋት በልዩ ትኩረት እየተሰራበት እንደሚገኝ አብራርተዋል።

የአዲስ መሶብ ዲጂታል የአንድ ማዕከል አገልግሎት መጀመር የህብረተሰቡን የዘመናት ምሬት በዘላቂነት የፈታ ሲሆን፣ በአገልግሎቱም የህዝቡን እርካታ በከፍተኛ ደረጃ ማሳደግ ተችሏል።

ይህ ዘመናዊ አሰራር ህዝቡ የሚፈልገውን አገልግሎት በአንድ ማዕከል በቀላሉ እንዲያገኝ በማድረግ በመንግስትና በህብረተሰቡ መካከል ያለውን የጋራ መተማመን ይበልጥ ማጎልበት መቻሉን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም