ቀጥታ፡

የአዲስ አበባ ሁለንተናዊ የልማት ስኬቶች ስምን ከግብር በማሰናሰል የተገኙ ውጤቶች ናቸው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ሁለንተናዊ የልማት ስኬቶች ስምን ከግብር በማሰናሰል የተገኙ ውጤቶች መሆናቸውን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ላለፉት ሶስት ተከታታይ ቀናት ሲያካሂድ የቆየውን የ2018 በጀት ዓመት እና የአምስት ዓመት ስትራቴጂካዊ ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ በስኬት አጠናቋል።


 

የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ የከተማ አስተዳደሩ በ2018 በጀት ዓመት ከ96 በመቶ በላይ የአፈጻጸም ውጤት አስመዝግቧል። 

በመዲናዋ በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊ፣ በፖለቲካዊ እና በሌሎች ዘርፎች የተመዘገቡት ስኬቶች ከተማዋን ውብና ጽዱ ከማድረጋቸውም በላይ ዓለም አቀፍ እውቅና ጭምር እንዳስገኙ ገልጸዋል። 

የኑሮ ውድነትን በማረጋጋት፣ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን በማሳካት፣ እንዲሁም ግልጽነትና ተጠያቂነትን በማስፈን የዜጎችን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ መቻሉንም አስታውቀዋል።

የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር ዓባይ በበኩላቸው፤ ባለፉት አምስት ዓመታት መዲናዋን ማራኪ ገጽታ በማላበስ ረገድ ሁለንተናዊ ስኬቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል። 

የተገኙት ውጤቶችም የሕዝብን ጥያቄዎች ምላሽ በማስገኘት እና ግዙፍ ፕሮጀክቶችን በጥራትና በፍጥነት በመፈጸም ረገድ የታየው የአመራር ቁርጠኝነት ውጤት መሆናቸውን አስረድተዋል። 

በቀጣይም የተገኙ ስኬቶችን በማስቀጠልና ክፍተቶችን በማረም የዜጎችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሥራዎች እንደሚከናወኑ አረጋግጠዋል።

በብልጽግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሞገስ ባልቻ በበኩላቸው፤ በ2018 በጀት ዓመት የከተማዋን እና የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልጽግና የሚያፋጥኑ ሥራዎች መሠራታቸውን ገልጸዋል። 

በቀጣይም የመዲናዋን በጎ ገጽታ በማጎልበት እና የሕዝቡን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ረገድ ተጨባጭ ውጤቶችን ማምጣት እንደሚገባ አስገንዝበዋል።

በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ሚሊዮን ማቴዎስ፤ በመዲናዋ የሚከናወኑ ቁልፍ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች ለዜጎች ሰፊ የሥራ ዕድል እየፈጠሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል። 

የኢንዱስትሪ፣ የከተማ ግብርና፣ የኮንስትራክሽንና የአገልግሎት ዘርፎች የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ረገድ ያላቸው ፋይዳ ከፍተኛ እንደሆነም አክለዋል።

በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የፐብሊክ ሰርቪስና ሰው ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ጀማሉ ጀምበር (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የዲጂታል መንግሥት አገልግሎት የተገልጋዮችን እርካታ እያሳደገ መሆኑን ገልጸዋል። 

በቀጣይም በአንድ ማዕከል አገልግሎት የተጀመረውን የዘመናዊ አሠራር አቅም ይበልጥ በማጠናከር ተደራሽነቱን እንደሚያሰፉ አስረድተዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም