ቀጥታ፡

ባለፉት አምስት ዓመታት አዲስ አበባን የሰላምና የልማት ማዕከል ማድረግ ተችሏል – ከንቲባ አዳነች አቤቤ

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 10/2018(ኢዜአ)፦ ባለፉት አምስት ዓመታት ስር የሰደዱ ችግሮችን በመቅረፍ አዲስ አበባን የሰላምና የልማት ማዕከል ማድረግ መቻሉን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የ2018 በጀት ዓመት ማጠቃለያ የስራ አፈጻጸም ግምገማ ማካሄድ ጀምሯል።


 

ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር፤ በበጀት ዓመቱ ለመፈጸም የተቀመጡ ግቦች እንዲሁም የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ እቅድ አፈጻጸም እንደሚገመገም ገልጸዋል።

ከንቲባዋ ባለፉት አምስት ዓመታት የተያዙ ስትራቴጂክ ግቦችን በተሟላ ሁኔታ በመተግበር በርካታ ውጤቶች መመዝገባቸውን ተናግረዋል።

በአዲስ አበባ ስር የሰደዱ ችግሮችን በመፍታትና ስር ነቀል የአስተሳሰብ ለውጥ በመፍጠር ከተማዋን የሰላምና የልማት ማዕከል ማድረግ መቻሉን ጠቁመዋል።

አዲስ አበባ ማህበራዊ ፍትህ የነገሰባት፣ ጽዱ፣ አረንጓዴና ውብ ከተማ እንድትሆን የተሰሩ ስራዎች ከተማዋ የዓለምን ትኩረት እንድትስብ ማስቻሉን ጠቅሰዋል።

በርካታ ስኬቶች ቢመዘገቡም አሁንም ያልተሻገርናቸው ተግዳሮቶች አሉ ያሉት ከንቲባዋ፣ የአመራሩ የአፈጻጸም ልዩነት እንዲሁም የኑሮ ውድነት ጉዳይ በጥልቀት እንደሚገመገም ተናግረዋል።

ከሕዝቡ የመልማት ፍላጎትና ከብልጽግና ግብ አንጻር በርካታ ቀሪ ስራዎች እንዳሉ አመላክተው፣ ስኬቶችን በማስፋት እንዲሁም ተግዳሮቶችን ለይቶ በመፍታት የላቀ አፈጻጸም ለማስመዝገብ መትጋት እንደሚገባ አስገንዝበዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም