ቀጥታ፡

ሀገራዊ የኢኮኖሚ ሽግግርን የሚያረጋግጥ ብቁና ተወዳዳሪ የሰው ኃይል ማፍራት ትኩረት ተሰጥቶታል

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 10/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የጀመረችውን ሁለንተናዊ የኢኮኖሚ ሽግግር የሚያረጋግጥ በዕውቀትና በክህሎት የዳበረ፣ ብቁና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሰው ኃይል ማፍራት ቁልፍ ተግባር ተደርጎ እየተሠራበት መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተሻለ በሬቻ (ዶ/ር) ገለጹ።   

የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተሻለ በሬቻ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የሥራ ዕድል ፈጠራን ለማጠናከርና የኢንዱስትሪዎችን የሰው ኃይል ፍላጎት ለማሟላት በፖሊሲና በስትራቴጂ ሰፊ የማሻሻያ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው።

የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራን በመከተል ዜጎች በቂ የኢንተርፕረነርሺፕ ዕውቀትና ክህሎት ጨብጠው ወደ ሥራ እንዲገቡ እየሰራ ይገኛል ብለዋል።

ቀጣይነት ባለው ሁኔታ ሥልጠናዎችን ከገበያ ተጨባጭ ፍላጎት ጋር በማጣጣም ውጤታማ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ የኢኮኖሚ ሽግግር የሚያሳካ፣ ዘመኑን የዋጀ እውቀትና ክህሎት የቀሰመ የሰው ኃይል ማፍራት ልዩ ትኩረት እንደተሰጠውም ጠቁመዋል።

ሥልጠናዎች ከንድፈ ሀሳብ ወጥተው በብቃትና በተግባር ላይ የተመሠረቱ እንዲሆኑ ሰፊ የሥርዓተ-ትምህርት ማሻሻያ እየተደረገ ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፥ ከአዳዲስ ቴክኖሎጂዎች ጋር ማስተሳሰር ቅድሚያ የሚሰጠው ተግባር መሆኑን ጠቅሰዋል።

መንግሥት በክህሎት ልማት ረገድ የጀመረውን ተግባር ይበልጥ ለማጠናከር የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው፥ በመላ ሀገሪቱ የግል ዘርፉን ጨምሮ ከ1 ሺህ 500 የቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ኮሌጆች መኖራቸውን ተናግረዋል።

የማሰልጠኛ ተቋማቱ ከኢንዱስትሪው ፍላጎት ጋር በቀጥታ ትስስር እንዲፈጥሩ እየተደረገ እንደሚገኝም አመላክተዋል።

ኢትዮጵያውያን ወጣቶች የፈጣን የቴክኖሎጂ ዕድገት ተጠቃሚና ተዋናይ እንዲሆኑ ለማስቻል ሰፊ የዲጂታል ክህሎት ሥልጠናዎች በሁሉም የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ውስጥ እንዲካተቱ መደረጉን አንስተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም