ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሞሪሸስ የቀጥታ በረራ አገልግሎት አህጉራዊ የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያፋጥን ነው 

አዲስ አበባ፤ሐምሌ 9 /2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሞሪሸስ የቀጥታ በረራ አገልግሎት አህጉራዊ የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያፋጥን መሆኑን የሞሪሸስ ፕሬዝዳንት ዳህራምቢር ጎኩል ገለጹ።

የቀጥታ በረራ አገልግሎቱ የቱሪዝም፣ የንግድ፣ የኢንቨስትመንትና የሰው ኃይል ልማት ዕድሎችን የሚያሰፋ መሆኑን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከሐምሌ 5 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በአዲስ አበባና በፖርት ሉዊስ መካከል በሳምንት ሦስት ጊዜ የሚደረግ ቀጥታ የመንገደኞች በረራ በይፋ አስጀምሯል።


 

የሞሪሺየስ ፕሬዝዳንት ዳህራምቢር ጎኩል የአየር መንገዱን የቀጥታ በረራ መጀመር አስመልክቶ ለፐልስ ኦፍ አፍሪካ ሚዲያ (Pulse of Africa Media POA) እንደገለጹት፤ ጠንካራ የአየር ትስስር የአፍሪካን የኢኮኖሚ አቅም ለማጎልበት ወሳኝ ነው።

በአዲስ አበባና በፖርት ሉዊስ መካከል የቀጥታ በረራ መጀመሩም፣ የአፍሪካ ኅብረት የአህጉራዊ ኢኮኖሚ ውህደትን የማፋጠን ራዕይ በማሳካት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ ገልጸዋል።

ኢትዮጵያም በአቪዬሽን ዘርፍ የአፍሪካን የኢኮኖሚ ውህደት ለማፋጠን ቁልፍና ተግባራዊ እርምጃ እየወሰደች መሆኗን የሚያሳይ ጠንካራ መልዕክት እንደሚያስተላልፍ ጠቁመዋል። 

የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሞሪሸስ የበረራ አገልግሎትም፣ የሀገራቱን ታሪካዊ ግንኙነት የበለጠ በማጠናከር የኢኮኖሚ ትብብርን እንደሚያጎለብት አንስተዋል።

ሞሪሸስ ለዓለም አቀፍ ባለሃብቶችና ለንግድ ተቋማት ወደ አፍሪካ መግቢያ በር ለመሆን እየሠራች በመሆኗ፣ ጠንካራ የአየር ትስስርን ማጎልበት ጉልህ ፋይዳ እንዳለው ተናግረዋል።


 

የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአፍሪካና በዓለም ያለው ሰፊ የበረራ ተደራሽነት፣ በሀገራቱ መካከል የንግድና የኢንቨስትመንት ፍሰትን በእጅጉ በማሳደግ የሎጂስቲክስ ችግሮችን ለመቅረፍ እንደሚያስችል ገልጸዋል።

ከአቪዬሽን አገልግሎት ባሻገር፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በፓይለቶችና በሌሎች የአቪዬሽን ባለሙያዎች ስልጠና ያለውን ዓለም አቀፍ ተቀባይነት በመጥቀስ፣ ይህ ለሞሪሸስ ዜጎች ጠቃሚ ዕድል እንደሚፈጥር አስረድተዋል።

በቀጣይም በትምህርት፣ በጤና እና በሌሎች ዘርፎች ሀገራቱ በእውቀት፣ በቴክኖሎጂና በልምድ በመለዋወጥ ለሕዝቦቻቸው የጋራ ጥቅም የሚያስገኝ ሰፊ የትብብር አቅም እንዳለ ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም