ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ በመቅረጽ፣ ለአረንጓዴ ልማት ያላትን ቁርጠኝነት በተግባር አሳይታለች - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ በመቅረጽ፣ ለአረንጓዴ ልማት ያላትን ቁርጠኝነት በተግባር አሳይታለች
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 9 /2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ በመቅረጽ፣ ለአረንጓዴ ልማት ያላትን ፅኑ ቁርጠኝነት በተግባር ማሳየቷን የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፍቃዱ ፀጋ ገለጹ።
በኢትዮጵያ የአረንጓዴ አነስተኛና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንተርፕራይዞችን ማጠናከር ላይ ለተቀረጸው የምርምር ፕሮጀክት የተዘጋጀ የማስጀመሪያ አውደ ጥናት እየተካሄደ ይገኛል።
በአውደ ጥናቱ መክፈቻ ላይ የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፍቃዱ ፀጋ እንደተናገሩት፤ ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ በመቅረጽ፣ ለአረንጓዴ ልማት ያላትን ፅኑ ቁርጠኝነት በተግባር አሳይታለች።
ይህም በታዳሽ ኃይል መስፋፋት፣ በዘላቂ ግብርና እና ለአካባቢ ጥበቃ ተስማሚ በሆኑ የኢንዱስትሪ እንቅስቃሴዎች ውስጥ በግልጽ ይንጸባረቃል ብለዋል። አረንጓዴ ኢኮኖሚን መገንባት የመንግሥትን ጥረት ብቻ ሳይሆን የሁሉንም አካላት ንቁ ተሳትፎ እንደሚጠይቅም አንስተዋል።
በተለይም አነስተኛና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንተርፕራይዞችን ማሳተፍ ወሳኝና አማራጭ የሌለው ተግባር መሆኑን ገልጸው፤ እነዚህ ኢንተርፕራይዞች ለኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ሽግግር፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ለእሴት ሰንሰለት ዕድገት፣ ለሀገር ውስጥ ምርት እንዲሁም ለኢኮኖሚ ብዝኃነት ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳላቸው አስገንዝበዋል።
በርካታ አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች ወደ አረንጓዴ ልማት በሚያደርጉት ጉዞ ላይ ፈተናዎች እየገጠሟቸው እንደሚገኝም ጠቁመዋል።
ዛሬ ውይይት የሚደረግበት ፕሮጀክት በኢትዮጵያ የሚገኙ የአረንጓዴ ማኑፋክቸሪንግ ኢንተርፕራይዞችን በጥናትና ምርምር በመገምገም፣ በተጨባጭ መረጃ ላይ የተመሠረቱ ምክረ ሐሳቦችን እንደሚያቀርብ አስታውቀዋል።
የጥናቱ ዋና ዓላማ የኢንተርፕራይዞቹን የአረንጓዴ ሽግግር ወቅታዊ ሁኔታ፣ ዕድሎችና ፈተናዎች በግልጽ ማሳየት መሆኑን የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ፤ ለአረንጓዴ ኢንዱስትሪ ልማት የሚያስፈልጉ የፖሊሲ፣ የሕግ፣ የፋይናንስ እና የቴክኒክ ድጋፍ ማዕቀፎችን እንደሚለይም ጠቁመዋል።
ለኢንተርፕራይዞች ዕድገትና ተወዳዳሪነት የሚበጅ ምቹ ምህዳር ለመፍጠር፣ የእያንዳንዱ ባለድርሻ አካል የሥራ ድርሻና አስተዋፅኦ ምን መሆን እንዳለበት በጥናቱ በጥልቀት እንደሚፈተሽም አብራርተዋል።