ቀጥታ፡

የከተማዋን የገቢ አቅም በማሳደግ የህብረተሰቡን ጥያቄ ለመመለስ እየተሰራ ነው

ሰመራ፤ ሐምሌ 7/2018(ኢዜአ)፦ የገቢ አቅምን በማሳደግ ህብረተሰቡ ለሚያነሳቸው የልማት ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኢንጂነር አህመድኑር ሳሊም ገለጹ ።

የሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ቢሮ ጋር በመተባበር የገቢና የአስተዳደር ብቃት አቅምን ለማሳደግ የሚያስችል የስልጠናና የልምድ ልውውጥ መድረክ እያካሄደ ነው።


 

የሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኢንጂነር አህመድኑር ሳሊም በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የገቢ አቅምን በማሳደግ ማሕበረሰቡ የሚያነሳቸውን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ ለሚያስችሉ ተግባራት ትኩረት ተሰጥቷል።

በተለይ ለህብረተሰቡ የሚሰጡ አገልግሎቶችን  በማሻሻል የከተማዋን የመሠረተ ልማት ፍላጎት ለማሟላት የሚያስችሉ ስልቶች ተነድፈው ተግባራዊ መደረጋቸውን ነው የገለጹት።

በዛሬው እለት የተጀመረው ስልጠና እና የልምድ ልውውጥም ከተማዋ የገቢና ወጪ ኮሪደር ከመሆኑዋ ጋር ተያይዞ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎቱን የተመቸ ከማድረግ አንፃር ልምድ የሚቀመርበት መሆኑን ገልፀዋል። 

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ቢሮ የትምህርትና ስልጠና ዳይሬክተር ወይዘሮ አስቴር ተሰማ በበኩላቸው ፤በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የገቢ አቅምን አሟጦ በመጠቀም የህብረተሰብ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ ተችሏል።


 

ከስድስት የተመረጡ የአፍሪካ ከተሞች በፕሮጀክት አፈፃፀም አንደኛ በመሆን እንደተመረጠች እና አስተዳደሩ ይሕንን ልምድ ተግባራዊ ማድረግ እንደሚያስፈልገው ነው የተናገሩት።

ከተማ አስተዳደሩ የገቢ አቅሙን በማሳደግ  የኮሪደር ልማትን ጨምሮ አገልግሎት መስጫ ተቋማትን በስፋት ለማልማት እንደቻለም አመልክተዋል።

የገቢ አቅም ማሳደግ በሚፈለገው መልኩ መሠረተ ልማቶችን ለመገንባት እና ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል በመሆኑም  ይሕንንም እንደ ልምድ ወስዶ መስራት እንደሚገባ አሳስበዋል።

በስልጠናውና በልምድ ልውውጡ  በታክሰ መረጃ አሰባሰብ፣ በኦዲት ፣ በገቢ ግብር አዋጅ ፣በተጨማሪ እሴት ታክስ አዋጅና በሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ላይ  ያሉ መመሪያዎች እና አሰራሮች  በዝርዝር እንደሚዳሰሱም ነው የገለጹት።

ለሶስት ቀናት በሚቆየው የልምድ ልውውጥና ስልጠና ላይም  የሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር  የስራ ኃላፊዎችና ከፍተኛ ባለሙያዎች በመሳተፍ ላይ ናቸው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም