ቀጥታ፡

የደብረ ማርቆስ አውሮፕላን ማረፊያ ለጥያቄዎቻችን ምላሽ የሰጠ ነው- ነዋሪዎች

ደብረ ማርቆስ ፤ ሐምሌ 7/2018(ኢዜአ)፦ የደብረ ማርቆስ ንጉስ ተክለ ሃይማኖት አውሮፕላን ማረፊያ መገንባት ለመሰረተ ልማት ጥያቄዎቻችን ምላሽ የሰጠና ለአካባቢው ሁለንተናዊ እድገት ብሩህ ተስፋ የሰነቀ ነው ሲሉ የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የደብረ ማርቆስ ንጉስ ተክለ ሃይማኖት አውሮፕላን ማረፊያን ከቀናት በፊት መርቀው አገልግሎት አስጀምረዋል።

በዚሁ ሁነት ላይ ባስተላለፉት መልእክትም የአውሮፕላን ማረፊያው ተመርቆ ለአገልግሎት መብቃቱ የደብረ ማርቆስ ከተማና አካባቢውን ነዋሪዎች የዘመናት ጥያቄ የመለሰ መሆኑን ገልጸዋል።


 

ለ30 ዓመታት ተቋርጦ የቆየው ኤርፖርት ግንባታው ተጠናቆ ስራ መጀመሩ የአካባቢውን የንግድ፣ የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም እንቅስቃሴ በከፍተኛ ሁኔታ በማነቃቃት ለኢኮኖሚ ዕድገት አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ይሆናል ብለዋል።

አስተያየታቸውን የሰጡ የደብረ ማርቆስ ከተማ ነዋሪዎች፤ የአውሮፕላን ማረፊያው መገንባት ለልማት ጥያቄዎቻችን ምላሽ የሰጠና ለአካባቢው ሁለንተናዊ እድገት ብሩህ ተስፋ የሰነቀ ነው ሲሉ ተናግረዋል።

ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል አቶ የቆየ ዓለሙ፤ የአውሮፕላን ማረፊያው ስራ መጀመር የለውጡ መንግስት የነዋሪውን ለዘመናት የቆየ የመሰረተ ልማት ጥያቄ ምላሽ የሰጠ በመሆኑ ከፍተኛ ደስታ ተሰምቶናል ብለዋል።

የኔፋንታ ተገኝ እና ጥላሁን ፋንታሁን የተባሉ ነዋሪዎችም ፤ የአውሮፕላን ማረፊያ መገንባቱ የደብረማርቆስ ከተማና አካባቢው ሕዝብ ለረጅም አመታት ሲያቀርበው ለነበረው የመሰረተ ልማት ጥያቄ ምላሽ የሰጠ መሆኑን ገልጸዋል።

በተለይም ለሕክምና ፣ ለንግድና ለሌሎች አስቸኳይ ጉዳዮች ወደ አዲስ አበባ የሚደረጉ ፈጣን ጉዞዎችን ለማድረግ ሁነኛ መፍትሄ በመሆኑ ተደስተናል ብለዋል።

ወይዘሮ እኔምአየሁ ጌቴ እና አቶ ነብዩ ብርሃኑ፤ የአውሮፕላን ማረፊያው ግንባታ ተጠናቆ አገልግሎት መጀመሩ ለከተማዋና አካባቢው ህዝብ ትልቅ ስኬትና ደስታ መሆኑን ተናግረዋል።

የለውጡ መንግስት የህዝብን ጥያቄ በማድመጥ ለአውሮፕላን ማረፊያው ግንባታ ትኩረት በመስጠት ለስኬት በማብቃቱ የላቀ ምስጋና ይገባዋል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም