በዞኑ የተገነቡ አነስተኛ እና መለስተኛ የመስኖ ግድቦች የአርብቶ አደሩን ማህበረሰብ አደጋ የመቋቋም አቅም አሳድገዋል - ኢዜአ አማርኛ
በዞኑ የተገነቡ አነስተኛ እና መለስተኛ የመስኖ ግድቦች የአርብቶ አደሩን ማህበረሰብ አደጋ የመቋቋም አቅም አሳድገዋል
አዳማ፤ ሐምሌ 7/2018(ኢዜአ)፦ በቦረና ዞን የተገነቡ አነስተኛ እና መለስተኛ የመስኖ ግድቦች የአርብቶ አደሩን ማህበረሰብ አደጋ የመቋቋም አቅም መሳደጋቸውን የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አብዱሰላም ዋሪዮ ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሰሞኑን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ልማትን በማስመልከት በሰጡት ማብራሪያ ቀደም ሲል በድርቅ ይፈተን የነበረው የቦረና አካባቢ በአሁኑ ወቅት በስንዴ ልማት ትልቅ ስራ እየሰራ መሆኑን አንስተዋል።
የኦሮሚያ ክልል መንግስትም የአርብቶ አደሩን ማህበረሰብ ኑሮ ለማሻሻልና የእንስሳት ሀብቱን ከአደጋ ለመጠበቅ የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል።
ከዚህ ውስጥ የአርሶና አርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት ለመቀነስና የኑሮ ሁኔታን ለማሻሻል መለስተኛ እና አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ ዋነኛው ነው።
የክልሉ መንግስት 'ፊና' ብሎ በሰየመው የአነስተኛ እና መለስተኛ ግድቦች ግንባታ ፕሮጀክት ተጠቃሚ ከሆኑት ዞኖች መካከል የቦረና ዞን አንዱ ነው።
የቦረና ዞን ዋና አስተዳዳሪ አብዱሰላም ዋሪዮ፤ በዞኑ የአርብቶ አደሩን ድርቅ የመቋቋም አቅም ለማሳደግ እየተከናወኑ ባሉ ሥራዎች ውጤቶች እየተመዘገቡ ነው ብለዋል።
የቦረና ዞን ለዝናብ እጥረት እና ድርቅ የተጋለጠ መሆኑን አንስተው፣ የ'ፊና' ፕሮጀክት ተግባራዊ መሆን ከጀመረ ወዲህ ግን ይህ ችግር እየተፈታ መምጣቱን ገልጸዋል።
እስካሁን አገልግሎት መስጠት የጀመሩ የመስኖ ግድቦች የዝናብ ውሃን በመያዝ የዝናብ እጥረት በሚከሰትበት ጊዜ ጥቅም ላይ እንዲውል እየተደረገ የማህበረሰቡ የድርቅ አደጋን የመቋቋም አቅም እየተገነባ መሆኑን ጠቁመዋል።
በአሁኑ ወቅት በቦረና ዞን 18 የፊና ፕሮጀክቶች ውሃ በመያዝ አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኙ አስታውሰው በዚህም የአርብቶ አደሩ ማህበረሰብ የእንስሳት መኖ፣ አትክልትና ፍራፍሬ፣ ስንዴ እና የተለያዩ የሰብል ዓይነቶችን እያመረተ ይገኛል ብለዋል።
በተጨማሪም የመስኖ ግድቦቹን በመጠቀም የእንስሳት መኖ በማልማት፣ ድርቅ በሚከሰትበት ጊዜ እንስሳት ለችግር እንዳይጋለጡ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል ነው ያሉት።
እነዚህ ፕሮጀክቶች የአርብቶ አደሩን ማህበረሰብ አደጋን የመቋቋም አቅም ከማሳደግ ባለፈ፣ የሥራ ባህልን እየቀየሩ መሆኑንም አስረድተዋል።
የኦሮሚያ ክልል መስኖና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ መረጃ እንደሚያመለክተው በ'ፊና' ፕሮጀክት ስር 37 የመስኖ ግድቦች ተጠናቀው ለአገልግሎት በቅተዋል።
በዚህ ዓመትም በመስኖ ግድቦቹ 864 ሚሊየን ኪዩቢክ ሜትር ውሃ መያዝ በመቻሉ ሰፊ መሬት በመስኖ ማልማት መቻሉ ተመልክቷል።