ቀጥታ፡

በክልሉ በበጀት ዓመቱ 47 አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች ወደሥራ ገብተዋል

ሐረር፤ ሐምሌ 7/2018 (ኢዜአ)፡-በሐረሪ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 47 አዳዲስ አነስተኛ እና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች ወደ ሥራ መግባታቸውን የክልሉ ኢንተርፕራይዝ ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ አስታወቀ።

በክልሉ ለአምራች ኢንዱስትሪዎች በተፈጠረው ምቹ ሁኔታ ወደ ማምረት ሥራ የገቡ ፋበሪካዎች ለዜጎች የሥራ ዕድል እየፈጠሩ መሆኑም ተመላክቷል።

የክልሉ ኢንተርፕራይዝ ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ ሃላፊ ኡስማኢል ዩስፍ ለኢዜአ እንደገለጹት በክልሉ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ለማስፋፋት ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው።


 

በተለይም የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የአምራች ኢንዱስትሪውን የማምረት አቅም ከማሳደግ ባለፈ በዘርፉ ትልቅ መነቃቃት እየፈጠረ ይገኛል ብለዋል።

በተጠናቀቀው የ2018 በጀት ዓመት ሰባት መካከለኛ እና 47 አነስተኛ አዳዲስ ኢንዱስትሪዎች ወደሥራ እንደገቡ ገልጸው፣ ተጨማሪ 16 አዳዲስ ኢንዲስትሪዎች ደግሞ የግንባታ ሥራቸውን አጠናቀው ወደማሽነሪ ተከላ ሥራ መግባታቸውን ተናግረዋል።

እንደ ቢሮ ሀላፊው ገለጻ በክልሉ ወደሥራ የገቡት ኢንዱስትሪዎች ተኪ ምርቶችን በማምረት የውጪ ምንዛሬን ከማስቀረት አንጻር ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ ይገኛሉ።

አምራች ኢንዱስትሪዎቹ ከሃይል አቅርቦት፣ ከመሰረተ ልማት ጋር በተያያዘ ያሉባቸውን ችግሮች ለመፍታት መሰራቱን ገልጸው፣  ዘንድሮ  በኢንዱስትሪ ዘርፉ ብቻ  621 ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚ የሥራ እድል ተፈጥሯል ብለዋል።


 

በመንግስት የተፈጠረላቸውን ምቹ ሁኔታ ተጠቅመው በተደራጁበት የፈርኒቸር ሥራ ዘንድሮ ወደ ማምረት መሸጋገራቸውን የገለጸው ደግሞ ወጣት መሃዲ አብዱልዋሲ  ነው።

ወደፊት ምርታቸውን በጥራት በማምረት ወደ ውጭ የመላክ እቅድ መያዛቸውን ጠቁሞ፣ ከማህበሩ አባላት በተጨማሪ ለሌሎች ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውንም ተናግሯል።

የስንዴ ዱቄት በማምረት ለአካባቢው  እያከፋፈሉ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ በሐረር ከተማ ኢንዱስትሪ ዞን የሚገኘው የቀነኒ ፉድ ኮምፕሌክስ ፋብሪካ ሥራ አስኪያጅ አቶ ተስፋ አስፋው ናቸው። 


 

በአሁኑ ወቅትም  ዘመኑን የዋጀ  የማምረቻ ማሽን በከፍተኛ ወጪ ከውጭ አገር በማስመጣት የማስፋፊያ ሥራ እያከናወኑ መሆኑን ጠቁመዋል። 

የክልሉ መንግስት ለአምራች ኢንዱስትሪዎች የፈጠረው ምቹ ሁኔታ ስራቸውን ይበልጥ ተግተው እንዲሰሩ የሚያበረታታ መሆኑንም አክለዋል።

በፋብሪካው የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው መካከል ቢሻው ሃይሉ እንደተናገረው፣ በክልሉ የኢንዱስትሪዎች መስፋፋት የሥራ ዕድል ተጠቃሚነትን ከማጎልበት ባሻገር አዳዲስ የቴክኖሎጂ እውቀቶችን ለማሽጋገር እያገዘ ነው።

 

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም