በበጀት ዓመቱ ከ5 ሚሊዮን ለሚበልጡ ዜጎች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል - ኢዜአ አማርኛ
በበጀት ዓመቱ ከ5 ሚሊዮን ለሚበልጡ ዜጎች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል
ሀዋሳ፤ ሐምሌ 5/2018 (ኢዜአ)፡-በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ5 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩን የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ገለፀ።
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የሥራ ዕድል ፈጠራ ዘርፍ የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸምና የ2019 በጀት ዓመት የትኩረት አቅጣጫን አስመልክቶ በሀዋሳ ከተማ ዛሬ የውይይት መድረክ አካሂዷል።
በመድረኩ ላይ በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የሥራ፣ የሥራ ስምሪትና ገበያ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ እንዳሉት፣ በበጀት ዓመቱ በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገር የሥራ ሥምሪት 5 ነጥብ 6 ሚሊዮን ዜጎች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል።
በሀገር ውስጥ የሥራ ስምሪት በግብርና፣ በኢንዱስትሪና በአገልግሎት ዘርፍ ከ4 ነጥብ 9 ሚሊዮን በላይ ዜጎች የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ሲሆን ከ670 ሺህ በላይ ዜጎች ደግሞ በውጭ ሀገር የሥራ ዕድል ማግኘታቸውን ገልጸዋል።
ለኢንተርፕራይዞች በፋይናንስ አቅርቦት ላይ ያለውን ክፍተት ለመሙላት ከባንኮችና ጋር በቅንጅት በመሰራቱ በበጀት ዓመቱ 85 ቢሊዮን ብር የሚጠጋ የገንዘብ ብድር ለማቅረብ እንደተቻለም ተናግረዋል፡፡
እንደ አቶ ሰለሞን ገለጻ፣ የሥራ ዕድል ፈጠራን ለማስፋትም የቤተሰብና የማህበረሰብ ሀብቶችን ለሥራ ዕድል ፈጠራ ለማዋል በቁርጠኝነት ተሰርቷል።
ለሥራ ዕድል ፈጠራው ስኬትም ኢንተርፕራይዞችን የመደገፍ ፣ አዳዲስ የፈጠራ ሀሳቦችን የማበረታታትና ዲጂታል የሥራ መስኮችን የማስፋት ሥራ ትኩረት እንደተሰጠውም አስረድተዋል፡፡
በመድረኩ ላይ የተገኙት የኦሮሚያ ክልል ሥራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ዋሲሁን ጎልጋ በበኩላቸው፣ በክልሉ ያለውን የሥራ አቅም የመለየትና የሰው ኃይል ብቃት ላይ መሰራቱን ጠቅሰዋል፡፡
በዚህም በበጀት ዓመቱ ለ5 ነጥብ 8 ሚሊዮን ዜጎች የሥራ ፈጠራ ሥልጠናዎች መሰጠቱን አስረድተዋል፡፡
የሲዳማ ክልል ሥራ፣ ክህሎትና ኢንተርፕራይዝ ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ከፍያለው ከበደ በክልሉ የሥራ መስኮችን በማስፋት ስኬታማ ሥራዎች መከናወናቸውን ጠቅሰዋል።
ከባለድርሻ አካላት እና ከአጋር ድርጅቶች ጋር ተቀናጅቶ በመስራት የማምረቻና የመሸጫ ቦታ ችግር በመፍታት ለዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር መቻሉንም ጠቁመዋል፡፡
በመድረኩ የፌዴራል እንዲሁም የክልልና የከተማ አስተዳደሮች የዘርፉ ከፍተኛ አመራር አካላት ተገኝተዋል፡፡