የደብረ ማርቆስ ንጉሥ ተክለሃይማኖት አውሮፕላን ማረፊያ የሕዝቡን የተዳፈነ የዘመናት የልማት ጥያቄ የመለሰ ነው-ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ - ኢዜአ አማርኛ
የደብረ ማርቆስ ንጉሥ ተክለሃይማኖት አውሮፕላን ማረፊያ የሕዝቡን የተዳፈነ የዘመናት የልማት ጥያቄ የመለሰ ነው-ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
አዲስ አበባ ፤ሐምሌ 5 /2018 (ኢዜአ)፦የደብረ ማርቆስ ንጉሥተክለሃይማኖት አውሮፕላን ማረፊያ የሕዝቡን የተዳፈነ የዘመናት የልማት ጥያቄ የመለሰ ነው ሲሉ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለፁ፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)፣ የደብረ ማርቆስና የአካባቢው ሕዝብ ለዓመታት በጉጉት ሲጠብቀው የነበረውን፣ ለ30 ዓመታት ያህል ተቋርጦ የቆየውንና በአዲስ መልክ ተሻሽሎ ደረጃው ከፍ ብሎ የተገነባውን የደብረ ማርቆስ ንጉሥ ተክለሃይማኖት አውሮፕላን ማረፊያ ዛሬ በይፋ መርቀዋል።
የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ በምረቃው ወቅት እንደገለጹት፣ የአውሮፕላን ማረፊያው መገንባት ለአካባቢው ሁለንተናዊ ዕድገት ከፍተኛ ፋይዳ አለው።
ደብረ ማርቆስ ከ30 ዓመታት በፊት የአውሮፕላን ትራንስፖርት አገልግሎት ተጠቃሚ የነበረች ቢሆንም፣ ባለፉት ሦስት አሥርት ዓመታት ግን የአየር ትራንስፖርት አገልግሎቱን ተነፍጋ መቆየቷን አስታውሰዋል።
አካባቢው ከፍተኛ የግብርና ምርትና የኮንስትራክሽን ማዕድናትን ጨምሮ እምቅ የተፈጥሮ ሀብት ያለው በመሆኑ ሕዝቡ የአውሮፕላን ማረፊያ እንዲገነባለት ላለፉት 30 ዓመታት ያለማቋረጥ ሲጠይቅ መቆየቱን ጠቅሰዋል።
ሆኖም ከአዲስ አበባ ካለው ቅርብ ርቀትና ከተፈጥሮ ሁኔታዎች ጋር በተያያዘ አገልግሎቱን ማግኘት እንደማይቻል ከ20 ዓመታት በፊት በግልጽ ተነግሮት የነበረው ሕዝብ ተስፋ ቆርጦ እንደነበር አስታውሰዋል።
አሁን ግን የለውጡ መንግስት ይህንን አሉታዊ ምላሽ የቀየረ ዘመናዊ አውሮፕላን ማረፊያ ገንብቶ ለሕዝቡ ማስረከቡን የገለጹት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ ለዚህ ፕሮጀክት እውን መሆን ወሳኝ ሚና ላበረከቱት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ምስጋና አቅርበዋል።
ዛሬ የመረቅነው የትራንስፖርት መሠረተ ልማት ግለሰባዊና ማኅበራዊ ፋይዳው እጅግ ብዙ ነው፤ ተጋምዳ የኖረችውን ኢትዮጵያን የበለጠ ለማስተሳሰርና ማኅበራዊ ትስስርን ለማቀላጠፍ በእጅጉ ያግዛል ብለዋል።
ከአየር ማረፊያው መገንባት ጋር ተያይዞ ከክልሉ፣ ከዞኑና ከአካባቢው ማኅበረሰብ የሚጠበቁ ሁለት ዋና ዋና ጉዳዮችን አንስተዋል።
የመጀመሪያው የአካባቢውን ሰላም በጋራ መጠበቅ መሆኑን ገልጸው፤ በአሁኑ ወቅት በአማራ ሕዝብ ጥያቄ ስም ሕዝብን የሚያደናግሩና ከኢትዮጵያ ጠላቶች ጋር በመተባበር፣ ሕዝብን በዘረፋና በወንበዴነት የሚያሰቃዩ አጥፊ ኃይሎችን መታገልና ማስወገድ ከመንግሥት ባለፈ የኅብረተሰቡ ዋነኛ ኃላፊነት መሆኑን አስገንዝበዋል።
ሁለተኛው ጉዳይ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ሲሆን፤ የአየር ማረፊያው አንደኛው ግብ የምርትና የሰው እንቅስቃሴን ማቀላጠፍ በመሆኑ አርሶ አደሩና ባለሀብቶች በአካባቢው ያለውን እምቅ ሀብት አልምተው በጥራትና በብዛት ለሀገር ውስጥና ለዓለም ገበያ እንዲያቀርቡ አጽንኦት ሰጥተዋል።