የብዝሃ ኢኮኖሚ ልማት አቅጣጫን በመከተልና በተደመረ አቅም በማልማት ባለፉት አምስት አመታት የተመዘገበው ስኬት የሚደነቅ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የብዝሃ ኢኮኖሚ ልማት አቅጣጫን በመከተልና በተደመረ አቅም በማልማት ባለፉት አምስት አመታት የተመዘገበው ስኬት የሚደነቅ ነው
ሐረማያ፤ ሐምሌ 2/2018 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ የብዝሃ ኢኮኖሚ ልማት አቅጣጫን በመከተል አቅምን አካብቶ በተደመረ አቅም በማልማት ባለፉት አምስት አመታት የተመዘገበው ስኬት የሚደነቅ መሆኑን በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የግብርናና አካባቢ ሳይንስ ኮሌጅ ዲንና የአግሪካልቸራል ኢኮኖሚክስ ምሁር የሆኑት ከዲር ጀማል (ዶ/ር) ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 30ኛ መደበኛ ስብሰባ የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት አፈጻጸምን በተመለከተ ከምክር ቤት አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሁሉም ክልሎች በግብርና፣ ቱሪዝም፣ በመሠረተ-ልማትና በማህበራዊ ዘርፎች በተሰሩ ስራዎች ከፍተኛ ለውጥ እየመጣ መሆኑን ገልጸዋል።
እንዲሁም የወጪ ንግድ ገቢ 11 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን፤ በተለይም ከወርቅ 5 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር እና ከቡና 3 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር መገኘቱን አብራርተዋል።
ኢዜአ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ማብራሪያ ተከትሎ ያነጋገራቸው በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የግብርናና አካባቢ ሳይንስ ኮሌጅ ዲንና የአግሪካልቸራል ኢኮኖሚክስ ባለሙያ ከዲር ጀማል (ዶ/ር) ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች የሰጡትን ማብራርያ ስለመከታተላቸው ተናግረዋል።
በተለይም ሀገሪቱ ግብርናን በማስፋትና በማዘመን ከሚከናወነው ስራ በተጨማሪ በኢንዱስትሪና በሌሎች የሚከናወኑት ተግባራት አበረታች ውጤቶች ስለመመዝገባቸው ማንሳታቸውን ገልጸዋል።
ከለውጡ ማግስት በግብርናው ዘርፍ መሰረቱን በማስፋት የተከናወኑት ተግባራት ለሀገሪቱ ኢኮኖሚ እድገት፣ በስራ እድል ፈጠራና ድህነትን በመቀነስ ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን ተናግረዋል።
እንደ ዶክተር ከዲር ገለጻ፤ ቀደም ሲል ሀገሪቱ ካልተጠቀመችባቸው ዘርፎች መካከል ቱሪዝም መሆኑን በመጥቀስ ከለውጡ ወዲህ ትኩረት ተሰጥቶ የተከናወነውና ለውጥ የተመዘገበበት ዘርፉ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን አመልክተዋል።
በአሁኑ ወቅት በከተሞች የተገነቡት የኮሪደር ልማት ሰራዎች ቅርሶችን ከማደስና ከመጠበቅ ባሻገር በርካታ ሎጅ ተገንብተዋል፣ ሆቴሎች ተስፋፍተዋል፤ በዚህም የጎብኚው ቁጥር በመጨመር በዘርፉ የሚገኘው ገቢ እያጎለበተ ይገኛል ብለዋል።
ከመሰረተ ልማት ጋር በተያያዘም በኮሪደር ልማትና በሌሎች ኢኮኖሚውን አቅምና ፍሰት የሚያጎለብቱና መስተጋብሮችን በቀላሉ የሚያሳልጡ በርካታ ልማቶች መሰራታቸውን ተናግረዋል።
በዲጂታል መሰረተ ልማትም የተከናወኑ ተግባራት ኢትዮዽያን ወደ ተሟላ ዲጂታላይዜሽን ያሸጋገሩ ተግባራት ስለመከናወናቸው አንስተዋል።
ከለውጡ በፊት 2 ቢሊዮን ዶላር የነበረው ዓመታዊ የውጪ ንግድ ገቢ ባለፉት ዓመታት በተከናወነው ስራ ወደ 11 ቢሊዮን ዶላር ማደጉ መንግስት ምን ያህል የኢኮኖሚ መሰረቱን እንዳሰፋ የሚያሳይ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡