ቀጥታ፡

በአዲስ አበባ የቤት ኪራይ ጭማሪ ጣሪያ 11.5% ሆኖ ተወሰነ፤ የውል እድሳት ምዝገባም ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳል

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/2018(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ከተማ ለ2019 በጀት ዓመት የሚተገበረው ፍትሐዊ የቤት ኪራይ ዓመታዊ ጭማሪ ጣሪያ 11.5% ሆኖ መጽደቁን የአስተዳደሩ ቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ አስታወቀ።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የዜጎችን የኑሮ ጫና ለመቀነስ እና በኪራይ ገበያው ላይ የሚስተዋሉ ህገ-ወጥና ዘፈቀዳዊ አሰራሮችን በዘላቂነት ለመግታት ታላቅ እርምጃ መውሰዱን ቀጥሏል።

ከዚህ ቀደም በወጣው የቤት ኪራይ ቁጥጥር አዋጅ መሠረት፣ ለ2019 በጀት ዓመት የሚተገበረው ፍትሐዊ የቤት ኪራይ ዓመታዊ ጭማሪ ጣሪያ 11.5% ሆኖ መጽደቁን የቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ ገልጿል።

ይህንን ተከትሎ በመላው ከተማዋ የሚገኙ የግል መኖሪያ ቤቶች የአከራይ-ተከራይ አዲስ የውል እድሳት ምዝገባ ከዛሬ ሐምሌ 1 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በሁሉም ክፍለ ከተማ ቤቶች አስተዳደር ፅህፈት ቤት በይፋ መተግበር እንደሚጀመርም አስታውቋል።

ቢሮው እንዳመለከተው ፣ ይህ የዋጋ ማስተካከያ ውሳኔ በዘፈቀደ የተወሰነ ሳይሆን በከተማዋ ሰፊ ሳይንሳዊ ጥናት ተካሂዶ የነዋሪውን እውነተኛ የመክፈል አቅም ባገናዘበ መልኩ የተዘጋጀ መሆኑን ተመላክቷል።

ይህ አሰራር በአንድ በኩል አከራዮች ወቅቱንና የኢኮኖሚ ሁኔታውን ያገናዘበ ፍትሐዊ ገቢ እንዲያገኙ የሚያረጋግጥ ሲሆን፤ በሌላ በኩል ደግሞ ተከራዮች ከገቢያቸው ጋር የተመጣጠነ ኪራይ በመክፈል የተረጋጋ ሕይወት እንዲመሩ ያደርጋል ብሏል።

ውሳኔው ያለውን የኑሮ ጫና በከፍተኛ ደረጃ በመቀነስ ረገድ የጎላ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና መልካም አስተዳደር ፋይዳዎች እንዳሉት ቢሮው አረጋግጧል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም