ህገ-ወጡ የህወሃት ቡድን በትግራይ ክልል እያደረገ ያለውን የጦርነት ቅስቀሳና የግዳጅ ወታደራዊ ምልመላ በአስቸኳይ ሊያቆም ይገባል - ኢዜአ አማርኛ
ህገ-ወጡ የህወሃት ቡድን በትግራይ ክልል እያደረገ ያለውን የጦርነት ቅስቀሳና የግዳጅ ወታደራዊ ምልመላ በአስቸኳይ ሊያቆም ይገባል
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/2018 (ኢዜአ)፦ ህገ-ወጡ የህወሃት ቡድን በትግራይ ክልል እያደረገ ያለውን አዲስ የጦርነት ቅስቀሳና የግዳጅ ወታደራዊ ምልመላ በአስቸኳይ ሊያቆም እንደሚገባ የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎችና የማህበራዊ ሚዲያ አንቂዎች ጠየቁ፡፡
ሴንተር ፎር ሪስፖንሲብል ኤንድ ፒስፉል ፖለቲክስ (CRPP) ከትግራይ ብሮድካስቲንግ ሰርቪስ (TBS) ጋር በመተባበር ”ሰላም፣ ዴሞክራሲና ልማት በትግራይ፣ የመገናኛ ብዙኃን እና የማኅበረሰብ አንቂዎች ሚና” በሚል ርዕስ የውይይት መድረክ አካሂዷል።
የውይይቱን መጠናቀቅ ተከትሎ ባለ 14 ነጥብ የአቋም መግለጫ አውጥተዋል።
የመድረኩ ተሳታፊዎች ባወጡት የአቋም መግለጫ በትግራይ ክልል እየተፈጸመ ያለው የግዳጅ ወታደራዊ ምልመላና አፈና በአስቸኳይ እንዲቆም የጠየቁ ሲሆን፤ አካባቢውን ወደ አዲስ የጦርነት አዙሪት የሚገፉ ማናቸውም እንቅስቃሴዎች እንዲገቱ አሳስበዋል።
በትግራይ ክልል ወጣቶች ላይ እየተፈጸመ ያለው አፈና እና የግዳጅ ወታደራዊ ምልመላም በአስቸኳይ እንዲቆም በጽኑ ጠይቀዋል።
የመሬት ላይ እውነታው የትግራይ ወጣቶች ለተደጋጋሚ መክሸፍና ለከፋ እልቂት ሲዳረጉ መቆየታቸውን የጠቀሰው የአቋም መግለጫው፤ ይህ ታሪካዊ ምዕራፍ በአስቸኳይ ሊያበቃ እንደሚገባና ለዚህ መርህ መከበርም ባለሙያዎች በሙሉ አቅማቸው እንደሚሠሩ አስታውቋል።
የጋዜጠኞች፣ የዲጂታል ይዘት ፈጣሪዎችና የአክቲቪስቶች አጀንዳዎች በሙሉ በሕዝቡ እውነተኛና አንገብጋቢ ፍላጎቶች ላይ ብቻ እንዲያተኩሩ ጥሪ ቀርቧል።
የጦርነት ጋዜጠኝነትን እና ቀስቃሽ ፕሮፓጋንዳዎችን፣ የጥላቻ ንግግሮችና የተሳሳቱ መረጃዎችን፣ የሕዝብ አስተያየትን ለቡድን ፍላጎት የማጭበርበር ተግባራትን ማውገዝ እንደሚገባ በአቋም መግለጫው ተመላክቷል።
በዚህም የሕዝቡ ጥልቅ ሥቃይ ከፖለቲካ መፈክሮችና ከወታደራዊ ንግግሮች በስተጀርባ ሊደበቅ እንደማይገባ በአቋም መግለጫው ተገልጿል።
የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮችን በዘላቂነት መመለስና መልሶ ማቋቋም፣ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ፣ የጤና እና የትምህርት አገልግሎቶችን በይፋ ማግኘት፣ የመንግሥት ሠራተኞች የተከማቸ ደመወዝ ክፍያ መፈጸም እና የኢኮኖሚ ማገገም ላይ መገናኛ ብዙኃን በትኩረት ሊሠሩባቸው የሚገቡ ጉዳዮች እንደሆኑም ተመልክቷል።
የትግራይ የፖለቲካ ቡድኖች የሕዝቡን ሕልውና ከፓርቲ ፍላጎት በላይ እንዲያስቀድሙ፣ ቀጣናውን ወደ አዲስ ጦርነት ከሚገፋፉ ቅስቀሳዎች እንዲቆጠቡና ልዩነቶችን በሰላማዊ ውይይት ብቻ እንዲፈቱ ተጠይቋል።
የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ መንግሥት የሰላም ስምምነቶች መፈጸማቸውን እንዲያረጋግጥ፣ ተፈናቃዮችን ለመመለስና ወጣቶችን ከአዲስ ወታደራዊ ቅስቀሳ ለመጠበቅ በሕገ-መንግሥታዊና ሞራላዊ ሥልጣኑ አስቸኳይ እርምጃ እንዲወስድ ጥሪ ቀርቧል።
ለዚህም የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት መሪዎችና የሲቪል ማኅበረሰብ ተዋናዮች በሂደቱ እንዲሳተፉ ተጠይቋል። “ወደ ጦርነት መመለስ የለም! በሥቃይ ፊት ዝምታ አይኖርም! ሕዝብን ለፖለቲካ ወይም ለወታደራዊ ዓላማ መጠቀሚያ ማድረግ ይብቃ!” በማለት በአቋም መግለጫቸው አስገንዝበዋል።
የአቋም መግለጫው ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል፦
ሰላም፣ ዴሞክራሲና ልማት በትግራይ፡ የመገናኛ ብዙኃን እና የማህበረሰብ አንቂዎች ሚና
ሰኔ 30 2018 አዲስ አበባ
1. እኛ “ሰላም፣ ዴሞክራሲና ልማት በትግራይ፡ የመገናኛ ብዙኃን እና የማህበረሰብ አንቂዎች ሚና” በሚል መሪ ቃል በተካሄደው የውይይት መድረክ ላይ የተሳተፍን አካላት፤ በትግራይ ወቅታዊ የፖለቲካ፣ የፀጥታ፣ የሰብአዊ እና የልማት ሁኔታዎች ላይ በጥልቀት ከተወያየን በኋላ፣ ለትግራይ ሕዝብ፣ ለኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ እንዲሁም ለሰላም፣ ለዲሞክራሲ፣ ለሰብአዊ ክብር እና ለሀገራዊ መረጋጋት ካለን ጥልቅ የኃላፊነት ስሜት በመነጨ ይህንን የአቋም መግለጫ አውጥተናል።
2. የትግራይ ሕዝብ በጦርነት፣ በመፈናቀል፣ በኢኮኖሚ መቃወስ፣ በፀጥታ እጦት፣ በተቋማዊ አለመረጋጋት፣ በሰብአዊ ቀውስ እና በተራዘመ አለመተማመን ሳቢያ ከፍተኛ መከራ እያሳለፈ መሆኑን እንገነዘባለን። የትግራይ ሕዝብ ሕይወት፣ ክብር፣ ደኅንነት እና የወደፊት ዕጣ ፈንታ ከማንኛውም የፖለቲካ ስሌት፣ የቡድን ፍላጎት፣ የወታደራዊ ምኞት እና ከፋፋይ ትረካዎች በላይ ሊቀመጥ እንደሚገባ በጽኑ እናምናለን።
3. በተጨማሪም ሰላም አሁንም ተሰባሪ መሆኑን እና ወደ ማንኛውም የትጥቅ ግጭት መመለስ ለትግራይ ሕዝብ፣ ለኢትዮጵያ እንዲሁም ለሰፊው ቀጠና አስከፊ መዘዝ እንደሚያስከትል እንረዳለን። እናቶች፣ አባቶች፣ ወጣቶች፣ ሕጻናት፣ ተፈናቃይ ቤተሰቦች፣ የጦር ጉዳተኛ ዜጎች፣ ሥራ አጥ ምሩቃን፣ አርሶ አደሮች፣ የመንግሥት ሠራተኞችና ተጋላጭ የኅብረተሰብ ክፍሎች ቀደም ሲል ያሳለፉት ሥቃይ ሊደገም አይገባም። ምንም ዓይነት የፖለቲካ ዓላማ እንደገና ለሚመጣ ሥቃይ፣ ለግዳጅ ቅስቀሳ፣ ለጥላቻ ንግግር፣ ለማስፈራራት ወይም የሰላማዊ ድምጾችን ለማፈን ምክንያት ሊሆን አይችልም።
4. ስለሆነም ይህ መድረክ የሁሉም የፖለቲካ ተዋናዮች፣ የመገናኛ ብዙኃን ተቋማት፣ የማህበረሰብ አንቂዎች፣ የማህበረሰብ መሪዎች፣ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች እና በየትኛዉም እርከን ላይ ያሉ የመንግሥት ባለሥልጣናት ዋነኛ ኃላፊነት እንደገና ግጭት እንዳይቀሰቀስ መከላከል፣ ሰላማዊ ዜጎችን መጠበቅ፣ እውነትን ማስከበር፣ ዲሞክራሲያዊ ምህዳሩን መከላከል እና ሰላማዊ፣ ሕገ-መንግሥታዊና ሕዝብ-ተኮር የፖለቲካ ሂደትን መደገፍ መሆኑን ያውጃል።
5. ለመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች እና ለማህበረሰብ አንቂዎች የቀረበ ጥሪ፦ ሁሉም የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ጋዜጠኞች፣ አዘጋጆች፣ አሰራጮች፣ የዲጂታል ይዘት ፈጣሪዎች፣ የማህበረሰብ አንቂዎች እና የአስተያየት መሪዎች የጦርነት ጋዜጠኝነትን፣ ቀስቃሽ ፕሮፓጋንዳዎችን፣ የጥላቻ ንግግሮችን፣ የተሳሳቱ መረጃዎችን፣ የግዳጅ ንቅናቄ ትረካዎችን እና የሕዝብ አስተያየትን ለቡድን ፍላጎት ማጭበርበርን እንዲያወግዙና ውድቅ እንዲያደርጉ እንጠይቃለን። መገናኛ ብዙኃን የፍርሃት፣ የወታደራዊ አስተሳሰብ ወይም የማህበራዊ መከፋፈያ መሣሪያ መሆን የለባቸውም። ይልቁንም እውነትን፣ ሰላምን፣ ተጠያቂነትን፣ ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓትን፣ የሕዝብ ውይይትን፣ የሰብአዊ ንቃተ-ህሊናን እና ዲሞክራሲያዊ ኃላፊነትን በማስተዋወቅ ሕዝብን ማገልገል አለባቸው።
6. የሕዝብን እውነተኛ ስጋቶች ስለማንጸባረቅና የግዳጅ ምልመላን ስለማውገዝ፦ የመገናኛ ብዙኃን ተቋማት እና የማህበረሰብ አንቂዎች (አክቲቪስቶች) የሕዝቡን መሠረታዊና እውነተኛ ስጋቶች ድምፅ እንዲሆኑ አበክረን እናሳስባለን። በዚህ መሠረት፣ በምንም ዓይነት ሁኔታና ምክንያት በትግራይም ሆነ በሌሎች የኢትዮጵያ አካባቢዎች ወደ አዲስ የጦርነት አዙሪት የሚመራ ግጭት እንዳይቀሰቀስ ለመከላከል በጽኑ እንሠራለን።
6.1 የመሬት ላይ እውነታው እንደሚያሳየው፣ በተለያዩ ምክንያቶች የትግራይ ወጣቶች ለተደጋጋሚ መክሸፍና ለከፋ እልቂት ሲዳረጉ የቆዩበት ታሪካዊ ምዕራፍ በአስቸኳይ ሊያበቃ ይገባል። በመሆኑም፣ በምንም ዓይነት መስፈርት ተገቢነት፣ ሕጋዊ መሠረት እንዲሁም ሰብአዊ ክብር በሌለው መልኩ በትግራይ ክልል ወጣቶች ላይ እየተፈጸመ ያለው አፈና እና የግዳጅ ወታደራዊ ምልመላ (Forced Conscription) በአስቸኳይ እንዲቆም በጽኑ እንጠይቃለን፤ ለዚህም መርህ መከበር በሙያችንና በተሰማራንበት የማኅበራዊ መድረክ መስክ ሁሉ አስፈላጊውን ሁለንተናዊ ጥረት እናደርጋለን።
6.2 የመገናኛ ብዙኃን አጀንዳዎች በሙሉ በዋናነት በትግራይ ሕዝብ እውነተኛና አንገብጋቢ ፍላጎቶች ላይ ሊያተኩሩ ይገባል፤ እነኝህም፦ የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮችን በዘላቂነት መመለስ፣ የኑሮ መሠረቶችን ማደስ፣ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ፣ የጤና እና የትምህርት መሠረተ-ልማቶችንና አገልግሎቶችን በይፋ ማግኘት፣ የወጣቶች ደኅንነት ጥበቃ፣ የኢኮኖሚ ማገገም፣ የመንግሥት ሠራተኞች የተከማቸ ደሞዝ ክፍያ መፈጸም፣ በጦርነት የተጎዱ ማህበረሰቦችን መልሶ ማቋቋም፣ ማህበራዊ ፈውስ (Social Healing) እና የተጋላጭ ዜጎችን ሁለንተናዊ ደኅንነት መጠበቅ ናቸው። የሕዝቡ ጥልቅ ሥቃይና ዘላቂ ፍላጎት ከፖለቲካ መፈክሮች ወይም ከወታደራዊ ንግግሮች (Military Rhetoric) በስተጀርባ ሊደበቅ ወይም ሊታጠፍ አይገባም።
7. ለፖለቲካ ተዋናዮች የቀረበ ጥሪ፦ ሁሉም የትግራይ የፖለቲካ ተዋናዮችና ቡድኖች የሕዝቡን ሕልውና፣ ክብር እና የወደፊት ዕጣ ፈንታ ከፓርቲ ፍላጎት በላይ እንዲያስቀድሙ አበክረን እንጠይቃለን። ቀጠናውን ወደ አዲስ ጦርነት ሊገፋፉ ከሚችሉ ድርጊቶች፣ መግለጫዎች እና ቅስቀሳዎች እንዲቆጠቡ እናሳስባለን። በተጨማሪም የፖለቲካ ልዩነቶችን በውይይት፣ በሕጋዊ አካሄዶች፣ በሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓቶች እና በአካታች የዜጎች ተሳትፎ ሰላማዊ በሆነ መንገድ እንዲፈቱ ጥሪያችንን እናቀርባለን።
8. ለፌዴራል መንግሥት የቀረበ ጥሪ፦ የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ መንግሥት የትግራይ ሕዝብ ሥቃይ ለማቆም በሕገ-መንግሥታዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ዲፕሎማሲያዊ፣ ሰብአዊ፣ አስተዳደራዊ እና በሞራል ሥልጣኑ የተቻለውን ሁሉ እንዲያደርግ የጠነከረና አስቸኳይ ጥያቄ እናቀርባለን። የፌዴራል መንግሥቱ አዲስ ግጭትን ለመከላከል፣ ሰላማዊ ዜጎችን ለመጠበቅ፣ የሰብአዊ ድጋፍ ተደራሽነትን ለማስፋት፣ መልሶ ማገገምን ለመደገፍ፣ የሰላም ስምምነቶች መፈጸማቸውን ለማረጋገጥ እና በትግራይ ሕጋዊ፣ አካታችና ሰላማዊ አስተዳደር እንዲሰፍን ሁኔታዎችን ለማመቻቸት በአስቸኳይ፣ በጥበብ፣ በራስ የመግታት ስሜት፣ በርኅራኄ እና በኃላፊነት መንፈስ መንቀሳቀስ አለበት።
9. ልዩ ትኩረት የሚሹ ተግባራት፦ በተለይም የፌዴራል መንግሥቱ የሰላማዊ ዜጎችን ደኅንነትና ክብር ለማረጋገጥ፣ ያልተገደበ ሰብአዊ እርዳታን ለማመቻቸት፣ የአገር ውስጥ ተፈናቃዮችን መልሶ ለማቋቋም፣ መሠረታዊ አገልግሎቶችን ለመመለስ፣ የምግብ ዋስትና ምላሾችን ለማጠናከር፣ ወጣቶችን ከአዲስ ወታደራዊ ቅስቀሳ ለመጠበቅ እና ሰላማዊና ሕገ-መንግሥታዊ የፖለቲካ እልባት ለማምጣት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ያለውን ጥረት እንዲያጠናክር እንጠይቃለን።
10. የባለድርሻ አካላት ተሳትፎ፦ የፌዴራል መንግሥቱ እምነትን ለመገንባት፣ ውጥረትን ለመቀነስ እና ዘላቂ የሰላም ሂደትን ለመደገፍ የማህበረሰብ ሽማግሌዎችን፣ የሃይማኖት መሪዎችን፣ ሴቶችን፣ ወጣቶችን፣ የሲቪል ማህበረሰብ ተዋናዮችን፣ የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎችን እና ሕጋዊ ተቋማዊ አካላትን ጨምሮ ሁሉንም ሰላማዊ ባለድርሻ አካላት እንዲያሳትፍ እናሳስባለን። የሕዝቡ ሥቃይ የተራዘመ የፖለቲካ ድርድርን ሊጠብቅ አይችልም። አስቸኳይ እና ተግባራዊ እርምጃ ያስፈልጋል።
11. ለልማት አጋሮች እና ለማህበረሰቡ የቀረበ ጥሪ፦ የልማት አጋሮች፣ ሰብአዊ ድርጅቶች፣ የሲቪል ማህበረሰብ ተቋማት፣ የሃይማኖት መሪዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሴቶች ማህበራት፣ የወጣቶች ተወካዮች እና መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የትግራይ ሕዝብ ለሰላም፣ ለክብር፣ ለማገገም እና ለዲሞክራሲያዊ መረጋጋት የሚያቀርበውን ጥያቄ እንዲደግፉ እና ከጎኑ እንዲቆሙ ጥሪ እናቀርባለን። ለትግራይ የሚደረገው ድጋፍ ለሰላማዊ ዜጎች ጥበቃ፣ ለሰብአዊ ማገገም፣ ለተቋማዊ መደበኛ አሠራር፣ ለኑሮ መሠረት መታደስ፣ ለሥነ-ልቦና ፈውስ እና አዲስ ጦርነትን ለመከላከል ቅድሚያ መስጠት አለበት።
12. በማጠቃለያው፣ ሰላም ማለት ዝምታ ብቻ እንዳልሆነ ደግመን እናረጋግጣለን። ሰላም እውነትን፣ ፍትሕን፣ ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓትን፣ ዲሞክራሲያዊ ውይይትን፣ ተጠያቂነት ያለበትን አመራር እና ለሰው ልጅ ሕይወት ክብር መስጠትን ይጠይቃል። ፍርሃት በነገሠበት የሕዝብ ሕይወት ውስጥ ዲሞክራሲ ሊኖር አይችልም። የጦርነት ፉከራ በሕዝብ አገልግሎት ምትክ በሰፈነበት ቦታ ልማት ሊታሰብ አይችልም። የመገናኛ ብዙኃን ነፃነት ትርጉም የሚኖረው ሕዝብን ከተንኮል፣ ከጥላቻ እና ከዓመፅ ሲጠብቅ ብቻ ነው።
13. በዚህ መድረክ ማጠቃለያ ላይ፣ ኃላፊነት የተሞላበት ተግባቦትን፣ ለግጭት ተጋላጭ ያልሆነ (Conflict-sensitive) ጋዜጠኝነትን፣ በእውነታ ላይ የተመሰረተ ዘገባን፣ የዜጎች ትምህርትን እና ሕዝብ-ተኮር የውይይት ምህዳርን ለማሳደግ ቃል እንገባለን። ጦርነትን፣ የግዳጅ ምልመላን፣ ሳንሱርን፣ የጥላቻ ንግግርን እና የፖለቲካ ማስፈራራትን የተለመደ የሚያደርጉ ትረካዎችን ለመቋቋም ቁርጠኝነታችንን እንገልጻለን። መገናኛ ብዙኃንን እና አክቲቪዝምን ለሰላም፣ ለዲሞክራሲ፣ ለልማት፣ ለተጠያቂነት እና ለሰብአዊ ክብር መሣሪያ አድርገን ለመጠቀም እንስማማለን።
14. የትግራይ ሕዝብ ሰላም ይገባዋል ብለን እንያውጃለን። ደኅንነት ይገባዋል። ምግብ፣ መጠለያ፣ ትምህርት፣ ጤና ጥበቃ፣ የኑሮ መሠረት፣ ፍትሕና ተስፋ ይገባዋል። የሚጠብቀው አመራር፣ እውነትን የሚነግረው መገናኛ ብዙኃን እና የወደፊት ሕይወቱን የሚያገለግሉ ተቋማት ይገባዋል።
ይህ የአቋም መግለጫ የጋራ ጥሪያችን ነዉ፦
ወደ ጦርነት መመለስ የለም! በሥቃይ ፊት ዝምታ አይኖርም! ሕዝብን ለፖለቲካ ወይም ለወታደራዊ ዓላማ መጠቀሚያ ማድረግ ይብቃ! የትግራይ ሕዝብ ሥቃይ ሊቆም ይገባል፤ እያንዳንዱ ኃላፊነት ያለበት ተቋም አሁኑኑ እርምጃ መውሰድ አለበት። በትግራይ ሰላም፣ ዲሞክራሲና ልማት ላይ በተዘጋጀው የውይይት መድረክ ተሳታፊዎች የጸደቀ።
ሰኔ 30 2018 አዲስ አበባ