ቀጥታ፡

በሐረሪ ክልል በኮሪደር ልማቱ የተከናወኑት የቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ሥራዎች ጎብኚዎችን እየሳቡ ነው

ሐረር፤ ሐምሌ 1/2018(ኢዜአ)፦ በሐረሪ ክልል በኮሪደር ልማቱ የተከናወኑት የቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ተግባራት የቱሪስቶችን ፍሰት በከፍተኛ ሁኔታ እያሳደጉ መሆኑን በክልሉ በአስጎብኚነት የተሰማሩ ባለሙያዎች ገለጹ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) “ቱሪዝም አዲሱ የኢኮኖሚ ሞተር!” በሚል ሰሞኑን በሰጡት ማብራሪያ በዘርፉ የተከናወኑ ተግባራትንና የመጡ ውጤቶችን አንስተዋል።

የብዝሃ የኢኮኖሚ አማራጮችን መሰረት አድርጎ በመስራት በተለይም በቱሪዝም ዘርፍ የተመዘገበውን ስኬት በማሳያነት አቅርበዋል።

በሐረር የሚገኙ ጥንታዊ፣ ሃይማኖታዊና ታሪካዊ ቅርሶች እድሳትና የኮሪደር ልማትና ስራዎች ለቱሪዝም ዘርፉ እድገትና ማንሰራራት ትልቅ አቅም ከመሆናቸው ባለፈ ጎብኚዎችን እየሳቡ መሆኑ ተገልጿል።

የዘመናት ዕድሜ ያላቸው እነዚህ ቅርሶችን ከተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ አደጋዎች ለመታደግ በክልሉ መንግሥትና ባለድርሻ አካላት አማካኝነት የተቀናጀ የኮሪደር ልማት፣ የቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ሥራ ሲከናወን ቆይቷል።

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የጀጎልን ታሪካዊ ይዘት ሳይለቁ የተከናወኑ የጥገናና የማደስ ሥራዎች፣ የቱሪስት መናኸሪያዎችን የማስዋብ እንዲሁም የከተማዋን የምሽት ገጽታ የሚቀይሩ የኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶች የቅርሶቹን ዕድሜ ከማራዘም ባለፈ ለጎብኚዎች ምቹና ሳቢ አካባቢን መፍጠር ችለዋል።

ይህ አቀራረብ በተለይ የውጭና የሀገር ውስጥ ቱሪስቶች በከተማዋ የሚኖራቸውን ቆይታ እንዲያራዝሙና በባህላዊ እሴቶች ላይ ያላቸውን ልምድ እንዲያበለጽጉ ትልቅ ዕድል ፈጥሯል።

የቅርስ ጥበቃና ማሻሻያ ሥራዎቹ የክልሉን የቱሪዝም ገቢ ከማሳደግ ባለፈ፣ በቀጥታ በአስጎብኚነት፣ በሆቴል አገልግሎትና በባህላዊ እደ-ጥበብ ምርቶች ሽያጭ ላይ ለተሰማሩ የአካባቢው ማህበረሰብ አባላት ሰፊ የሥራ ዕድልና የገቢ ምንጭ በመሆን የላቀ ፋይዳ እያበረከተ ይገኛል።

በክልሉ በአስጎብኚ ስራ የተሰማራው ሐይሉ ጋሻው እንደሚገልጸው፤ የጀጎል ዓለምአቀፍ ቅርስን ጨምሮ በከተማና ገጠር ወረዳ የሚገኙ ታሪካዊና ጥንታዊ ቅርሶች የጥበቃና እንክብካቤ ሥራዎች ተሰርተዋል።

እነዚህ የቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ሥራዎች እንዲሁም ሸዋል ኢድን ጨምሮ የሚከናወኑ ክብረ በዓላት የሀገር ውስጥም ሆነ የውጪ ጎብኚዎችን በመሳብ በኩል አስተዋጽኦ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል።

በተለይም የቱሪዝም ዘርፉን ለማጎልበት የክልሉ መንግስት በተለያዩ አማራጮች ያከናወነው የማስተዋወቅ ስራ ባለሀብቶች በከተማው ሪዞርቶችና ሆቴሎች እንዲገነቡ እድል መፍጠሩንም ተናግሯል።

እንዲሁም በዘርፉ ለተሰማሩ ባለሙያዎች እየተሰጡ የሚገኙ ስልጠናዎችም ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ጠቁመዋል።

ሌላው አስጎብኚ ቴዎድሮስ በላይ በበኩሉ፤ በከተማው በኮሪደር ልማት የተከናወኑት ስራዎች በቱሪዝም ዘርፉ ላይ መነቃቃትን መፍጠሩንና ከተማዋን ውብና ጽዱ ከማድረግ ባለፈ ጎብኚው ተመልሶ እንዲመጣ እያስቻሉ መሆኑን ገልጸዋል።

በኮሪደር ልማት የተከናወኑት ስራዎች ቅርሶች ተጠብቀው እንዲቆዩና ለትውልድ እንዲተላለፉ ያስቻሉ መሆኑ አመልክተዋል።

በክልሉ ጎብኚው የሚያርፍባቸው ሆቴሎችና ሪዞርቶችን ከማስፋፋት አንጻር እየተከናወኑ የሚገኙ አበረታች ስራዎችም ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ጠቁመዋል።

የሐረሪ ክልል የቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር ሳሚ አብዱልዋሲ፤ በክልሉ በቱሪዘም ዘርፍ በተሰጠው ትኩረት የቱሪዝም መስህቦችን በማልማት፣ የጎብኚዎችን ቆይታ በማራዘምና ከዘርፉ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ አቅም በማሳደግ በኩል የተሻሉ ተግባራት መከናወናቸውን መግለጻቸው ይታወሳል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም