ቀጥታ፡

በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ግንባታቸው ተጠናቆ ወደ ሥራ የገቡ የልማት ተቋማት የህብረተሰቡን የልማት ጥያቄዎች የመለሱ ናቸው

ጭሮ፤ ሰኔ 30/2018(ኢዜአ)፡- በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ጭሮ ከተማ ግንባታቸው ተጠናቆ ወደ ሥራ የገቡ የልማት ተቋማት የረጅም ጊዜ የልማት ጥያቄዎችን የመለሱ መሆናቸውን የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ።

በከተማዋ ከ385 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነቡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች በዛሬው ዕለት ተመርቀዋል።


 

በፕሮጀክቶቹ ምረቃ ላይ የተገኙ የከተማዋ ነዋሪዎች ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ በአገልግሎት አሰጣጥ እና በመንገድ መሠረተ ልማት መስክ የነበሩባቸው ቅሬታዎችና ጥያቄዎች ምላሽ እያገኙ መሆኑን ተናግረዋል።

ከነዋሪዎቹ መካከል አቶ አብደላ ኢስማኤል እንዳሉት፤ የመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥ ያለመቀናጀትና ኋላቀር አሠራር ለእንግልትና ለተጨማሪ ወጪ ይዳርገን ነበር።

አሁን ግን የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት በከተማዋ በመጀመሩ አገልግሎቶችን በአጭር ጊዜ እንድናገኝ ስለሚያደርገን ትልቅ ደስታ ተሰምቶናል ብለዋል።

ሌላው ሼህ ኢስማኤል መሐመድ፣ በከተማዋ እየተካሄደ ያለው የኮሪደር ልማት የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ደረጃቸውን የጠበቁ የውስጥ ለውስጥና ዋና መንገዶች እንዲኖሩ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።

ቀደም ሲል በከተማዋ ምንም የመዝናኛ ስፍራ አልነበረም፤ በአሁኑ ወቅት ተመርቀው ለአገልግሎት የበቁት የመንገድ ዳር መናፈሻ ስፍራዎችና የሳይንስ ካፌ በተለይ ወጣቶች ከአልባሌ ቦታዎች እንዲርቁና በቂ መዝናኛ እንዲያገኙ ያደርጋል ብለዋል።

እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች የከተማዋን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ የሚያሳድጉና የረጅም ዓመታት የልማት ችግሮችን የፈቱ መሆናቸውን የጠቀሱት ደግሞ አባገዳ አሽም አብደላ ናቸው።

ወደ ፊትም ባላቸው አቅም ሁሉ ከልማቱ ጎን በመቆም የሚያደርጉትን ተሳትፎና ትብብር አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል።


 

የጭሮ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ መሐመድ ዑመር እንደገለጹት፤ በዛሬው ዕለት ተመርቀው ለአገልግሎት የበቁት ከ385 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነቡ 17 የልማት ፕሮጀክቶች ናቸው።

ፕሮጀክቶቹ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት፣ የኮሪደር ልማት፣ የመንገድ ዳር መዝናኛ ስፍራዎች እና የሳይንስ ካፌን ያካተቱ መሆናቸውን ገልጸዋል።

ከእነዚህም መካከል ከ100 ሚሊዮን ብር በሚሆን በጀት የተገነባው የአንድ ማዕከል አገልግሎት 68 የተለያዩ አገልግሎቶችን በአንድ ቦታ ማቅረብ የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል።

የምዕራብ ሐረርጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ወይዘሮ ኢክራም ጠሀ በበኩላቸው፤ በዞኑ የሕብረተሰቡን ዘርፈ ብዙ የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ የተገነቡ 24 የልማት ፕሮጀክቶች በዚህ ዓመት ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውን አስታውቀዋል።

እነዚህ የልማት ፕሮጀክቶች የመንገድ መሠረተ ልማት፣ የውኃ ተቋማት፣ ድልድዮች እና በአርብቶ አደር ወረዳዎች የተገነቡ የውኃ ግድቦችን ያካተቱ መሆናቸውን አመልክተዋል።

በተጨማሪም በዞኑ የጭሮን ከተማ ጨምሮ በመቻራ፣ ሂርና፣ ገለምሶ እና በዴሳ ከተሞችም በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተደገፉ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫዎች ለአገልግሎት ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸው፤ ኅብረተሰቡ በአካባቢው እየተገነቡ ባሉ የልማት ፕሮጀክቶች ላይ ተሳትፎውን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም