የቤት ልማት የመንግሥት አንኳር ፕሮጀክት ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) - ኢዜአ አማርኛ
የቤት ልማት የመንግሥት አንኳር ፕሮጀክት ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30/2018(ኢዜአ)፦ የቤት ልማት የመንግሥት አንኳር ፕሮጀክት ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ።
ባለፉት የለውጥ ዓመታት 1 ነጥብ 2 ሚሊየን ቤቶች መገንባታቸውንም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አስታውቀዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ተገኝተው፣ የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት የሥራ አፈጻጸምን በተመለከተ ከምክር ቤቱ አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል።
በማብራሪያቸውም የዜጎችን የመኖሪያ ቤት ጥያቄ ምላሽ መስጠት የሚያስችሉ ሰፊ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቅሰው፣ የቤት ልማት ጉዳይ ከጉባ ብስራቶች መካከል አንዱ መሆኑንና መንግሥት በከፍተኛ ትኩረት እንደሚሠራበት ተናግረዋል።
በዚህም መሠረት ባለፉት ሰባት ዓመታት ውስጥ ብቻ 1 ነጥብ 2 ሚሊየን ቤቶች መገንባታቸውን ጠቅሰዋል።
በቀጣዮቹ አምስት ዓመታትም 1 ነጥብ 5 ሚሊየን ቤቶችን በመንግሥት፣ በግል፣ በመንግሥትና በግል አጋርነት እንዲሁም በሌሎች አማራጮች ለመገንባት ዕቅድ ተይዞ ሰፊ እንቅስቃሴ እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል።
ይህንን ስኬታማ ማድረግ የሚያስችል አዲስ የመኖሪያ ቤት ፖሊሲ በሚኒስትሮች ምክር ቤት መጽደቁን ያነሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ግንባታውን በገጠርና በከተማ ለማፋጠን በትጋት እየተሠራ መሆኑን አስረድተዋል።
በቴክኖሎጂ የታገዘ የግንባታ ፍጥነትን ለመጨመርም እንደ 3ዲ ያሉ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ወደ ሥራ እየገቡ መሆኑን ገልጸዋል።
ከዚህም በተጨማሪ የግንባታ ግብዓት አቅርቦትን ለማስፋት በርካታ ፋብሪካዎች ወደ ሥራ እየገቡ ሲሆን፣ በዘርፉ የሚሰማሩ የኮንስትራክሽን ሠራተኞችም ተገቢውን ሥልጠና ወስደው ወደ ሥራ እየተሰማሩ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ቤት በአንድ ጊዜ መግዛት አቅም ለሌላቸው ወገኖችም በኪራይ ወይም ከወርሃዊ ገቢያቸው ላይ እየከፈሉ በረጅም ጊዜ የቤት ባለቤት መሆን የሚችሉበትን የሞርጌጅ ሥርዓት ለመዘርጋት መንግሥት በስፋት እየሠራበት መሆኑን አመላክተዋል።
የቤት ልማት የዜጎችን የአኗኗር ዘይቤ የሚያስተካክል፣ ሰፊ የሥራ ዕድል የሚፈጥርና የሀገሪቱን ኢኮኖሚ የሚያነቃቃ መሆኑን በማንሳት፤ መንግሥት ዘርፉን እንደ አንኳር የልማት ፕሮጀክት ወስዶ እየሠራበት እንደሚገኝና ውጤታማነቱም የጋራ ትጋትን የሚፈልግ መሆኑን አስገንዝበዋል።