ቀጥታ፡

የሀዋሳ ከተማ የኮሪደርና የሀይቅ ዳርቻ ልማት የጎብኚዎችን የቆይታ ጊዜ እያራዘመ ነው

ሀዋሳ ፤ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ) :- የሀዋሳ ከተማ የኮሪደርና የሀይቅ ዳርቻ ልማት የጎብኚዎችን ቀልብ በመሳብ የቆይታ ጊዜያቸውን እያራዘመው እንደሚገኝ የሲዳማ ክልል ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ ገለጸ።


 

በሲዳማ ክልል ታሪካዊና የተፈጥሮና የቱሪስት መስህቦችን በማልማትና በማስተዋወቅ ረገድ በተሰራው ሥራ፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ3 ሚሊዮን 280 ሺህ በላይ የሀገር ውስጥና የውጪ ቱሪስቶች ክልሉን መጎብኘታቸውን ቢሮው ገልጿል። 


 

የቢሮው ምክትል ኃላፊና የቱሪዝም ዘርፍ ኃላፊ አቶ አበበ ማሪሞ ለኢዜአ እንደገለፁት    የቱሪስት መስህቦችን በማልማት ኢኮኖሚያዊ ፋይዳቸውን ለማጉላት ሰፊ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ። 

ለዚህም በአብነትነት የሀዋሳ ፍቅር ሐይቅን፣ የጋራንባ ተራራ ባህላዊ ሎጅን፣ የሲዳማ አፊኒ ሶንጎ ባህላዊ የፍትሕ ሥርዓት ማከናወኛ ስፍራን፣ የተፈጥሮ ፍል ውኃ ስፍራዎችንና ፏፏቴዎችን ጠቅሰዋል።


 

በተለይም የሀዋሳ ከተማ የኮሪደር ልማትና የሐይቅ ዳርቻ ልማት የጎብኚዎችን የቆይታ ጊዜ በማራዘም ከዘርፉ የሚገኘው ገቢ እንዲጨምር ማድረጉን አቶ አበበ አንስተዋል። 

በዚህም በበጀት ዓመቱ ክልሉን ከ3 ሚሊዮን 280 ሺህ በላይ የሀገር ውስጥና የውጭ ቱሪስቶች መጎብኘታቸውንና ከዚህም 3 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን ገልጸዋል።


 

ከአዲስ አበባ ሀዋሳን ለመጎብኘት የመጡት አቶ ዘላለም ተስፋዬ በሰጡት አስተያየት፤ የሀዋሳ ከተማ ዕድገት፣ የኮሪደር ልማቱና የሐይቅ ዳርቻ ማሻሻያው የቱሪስቶችን ቀልብ መሳብ የሚችሉና ከተማዋን ተመራጭ መዳረሻ የሚያደርጉ መሆናቸውን ተናግረዋል።

የሀዋሳ ከተማን ለእረፍት ጊዜያቸው ዘወትር እንደሚመርጧት የገለጹት ደግሞ ሰላማዊት እሸቱ ናቸው። 


 

ለዚህም የከተማዋ ተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ የቱሪስት መዳረሻዎች፣ እንዲሁም የሐይቅ ዳርቻ ልማቱ ከተማዋን ይበልጥ ሳቢና ማራኪ እንዳደረጋትም አስረድተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም