ቀጥታ፡

በክልሉ  ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ 

ቦንጋ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የመሬት አያያዝና አጠቃቀምን በማሻሻል ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ፡፡

በቢሮው የተፈጥሮ ሀብት ልማትና መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም ዘርፍ የአየር ንብረት አፈፃፀም የመሬት አያያዝ ፕሮግራም (CALM) የመጀመሪያ ምዕራፍ መዝጊያ መርሃ ግብር አካሂዷል።


 

የክልሉ የግብርና ቢሮ ኃላፊ አማካሪና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዮሐንስ መላኩ፣ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል።

ለዚህም ያሉ የውሃ፣ መሬትና ሌሎች የተፈጥሮ ሀብቶችን መንከባከብ ማልማትና በተገቢዉ ጥቅም ለይ ማዋል ወሳኝ በመሆኑ የተለያዩ ፕሮጀክቶች ተቀርፀው በመተግበር ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል።

ከነዚህ ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ በሆነው (CALM)  በክልሉ በ40 ወረዳዎች በውሃና መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም ላይ በሰራው ስራ ምርት የማይሰጡ አሲዳማ መሬቶች እንዲያገግሙና ምርታማ እንዲሆኑ ትልቅ ሚና መጫወቱን ገልፀዋል።

በተጨማሪም በፕሮግራሙ እገዛ አርሶ አደሩ መሬቱን አስይዞ የብድርና ሌሎች አገልግሎቶችን  እንዲያገኝ የ2ኛ ዙር መሬት ልኬት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ነው የገለጹት፡፡

ክልሉ የበርካታ የተፈጥሮ ሀብቶች መገኛ በመሆኑ ይህን ሀብት በመንከባከብና ዘላቂነቱን ለማረጋገጥ የሁሉም ባለድርሻ አካላት ርብርብ ያስፈልጋል ብለዋል።

በፕሮግራሙ በ199 ተፋሰሶች ከ112 ሺህ 500 ሄክታር በላይ መሬት ማልማት 53 ሺህ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ማድረግ እንደተቻለ የገለጹት ደግሞ የክልሉ ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ውብሸት ዘነበ ናቸው ።


 

እንደ ክልል የመሬት ልኬት ከተካሄደባቸዉ 380 ሺህ ይዞታዎች ውስጥ 200 ሺህ ያህሉ በዚህ ፕሮግራም የተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል።

በቢሮው የፕሮጀክቱ አስተባባሪ አቶ ተረፈ ማሞ በበኩላቸዉ፣ በክልሉ ባለፉት ዓመታት በ40 ወረዳዎች በሁለት መቶ ተፋሰሶች ላይ ማህበራትን በማደራጀት ሲሰራ ቆይቷል ነው ያሉት።


 

በዚህም አርሶ አደሩ የተለያዩ ፍራፍሬዎችንና የውጭ ምንዛሬ የሚያስገኙ ሰብሎችን በማምረት ተጠቃሚ በመሆን ላይ እንደሚገኝ ነው የገለጹት።  

በመጀመሪያዉ ምዕራፍ ለተፋሰሱ አርሶ አደሮች ለኑሮ ማሻሻያና ለተለያዩ መሰረተ ልማት ግንባታዎች ከ247 ሚሊዮን ብር በላይ  ወጪ መደረጉን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም