ቀጥታ፡

በምስራቅ ወለጋ ዞን የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የልማት ፕሮጀክቶች አገልግሎት መስጠት ጀመሩ

ነቀምቴ ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ወለጋ ዞን የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በቅተዋል።

በዞኑ ጂማ አርጆ ወረዳ ከ749 ሚሊዮን ብር በላይ የወጣባቸው የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት በዛሬው እለት ተመርቀዋል።

በምረቃው ላይ የተገኙት የኦሮሚያ ክልል ውሃ እና ኢነርጂ ቢሮ አማካሪ ቡዛዮ ደገፉ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ግንባታቸው ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት የሆኑት እነዚህ ፕሮጀክቶች የህብረተሰቡን የረጅም ጊዜ ጥያቄ የሚመልሱ ናቸው።

ፕሮጀክቶቹ በተለይም የአገልግሎት አሰጣጡን የሚያቀላጥፉ እና የሚያዘምኑ ከመሆናቸው ባለፈ የተጀመረውን የብልጽግና ጉዞ ለማሳካት ትልቅ አስተዋጽኦ አላቸው ብለዋል።

የምስራቅ ወለጋ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ደሱ ለሚ በበኩላቸው፣ በዞኑ የህዝቡን የመልካም አስተዳደር፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥያቄዎች መመለስ የሚያስችሉ የልማት ስራዎች በስፋት እየተተገበሩ መሆኑን ገልጸዋል።

በዚህም በዞኑ የህዝቡን መሰረታዊ ጥያቄዎች የሚመልሱ ከ400 በላይ የተለያዩ የመሰረተ ልማት ስራዎች ተጠናቀው በሁለት ዙር እየተመረቁ ይገኛሉ ብለዋል።

በጅማ አርጆ ግንባታው ተጠናቆ የተመረቀው የንጹህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት አንዱ መሆኑን ጠቅሰው የማህበረሰቡን የረጅም ጊዜ ችግር በዘላቂነት የሚፈታ መሆኑን ገልጸዋል።

የጂማ አርጆ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ጥላሁን ተሰማ እንደገለጹት፤ በወረዳው ብቻ 21 የሚደርሱ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች በ749 ሚሊዮን ብር ግንባታቸው ተጠናቆ ለምርቃት በቅተዋል።

የህዝቡን ፍላጎት ለማሟላት የተደረገው የቅርብ ክትትል ፕሮጀክቶቹ በፍጥነት እንዲጠናቀቁ ከማድረጉም በላይ፣ የነዋሪዎችን የዕለት ተዕለት ኑሮ እያቃለለ መሆኑን ጠቁመዋል።

የአካባቢው ነዋሪዎችም በተከናወኑት የመሰረተ ልማት ስራዎች ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማቸው ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም