የቱሪዝም ዘርፉን እድገት ለማጎልበት የተቋማትን ቅንጅታዊ አሠራር ማጠናከር ወሳኝ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የቱሪዝም ዘርፉን እድገት ለማጎልበት የተቋማትን ቅንጅታዊ አሠራር ማጠናከር ወሳኝ ነው
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦የቱሪዝም ዘርፉን እድገት ለማጎልበት ወሳኝ የሆነውን የተቋማትን ቅንጅታዊ አሰራር የማጠናከር ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ የፌደራል ቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ገለጸ።
ኢንስቲትዩቱ ከደባርቅ ዩኒቨርሲቲና ከሰመራ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር "በዳሎል-ራስ ዳሽን ኮሪደር የማይበገር ቱሪዝም መገንባት” በሚል መሪ ሀሳብ የቱሪዝም ዕድሎችን በጥናት ለመለየትና ጠንካራ የቱሪዝም ሥርዓት ለመዘርጋት የሚያስችሉ ስትራቴጂካዊ ግብዓቶች ላይ ያተኮረ ዓውደ ጥናት አካሂዷል።
የፌዴራል ቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ይታሰብ ስዩም እንደገለጹት፤ የቱሪዝም ዘርፉን ለማሳደግ በርካታ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ።
ለዘርፉ የላቀ ውጤታማነት የተቋማትና የባለድርሻ አካላት ቅንጅትና ትብብር አስፈላጊ ነው ብለዋል።
ይህም የሀብት ብክነትን በመቀነስ፣ የእውቀትና ቴክኖሎጂ ሽግግርን በማሳደግ የማህበረሰቡን እንዲሁም የሀገሪቱን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እንደሚያስችል ነው የገለጹት።
የደባርቅ እና ሰመራ ዩኒቨርሲቲዎች ከትኩረት መስካቸው መካከል አንዱ የቱሪዝም ዘርፍ በመሆኑ በጋራ በመስራት የምርምር፣ የጥናትና የእውቀት ሽግግር ስራዎችን ማጠናከር እንዲሁም ሀብትን በብቃት መጠቀምን ያለመ ኢኒሼቲቭ መጀመሩን ገልጸዋል።
በኢኒሼቲቩም በዓለም ከባህር ጠለል በታች ዝቅተኛውና ሞቃታማውን ዳሎል እንዲሁም ረጅሙንና በቅዝቃዜው የሚታወቀውን የራስ ዳሽን ኮሪደርን እንደ አዲስ የቱሪዝም ብራንድ ለማስተዋወቅ እንደሚሰራ ተናግረዋል።
አካባቢዎቹ የእምቅ ተፈጥሯዊና ባህላዊ ሀብቶች መገኛ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል።
የማህበረሰቡን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ባረጋገጠ መልኩ በአካባቢው ያሉ የቱሪዝም ቁልፍ ተግዳሮቶችን የመለየትና በጥናትና ምርምር የመፍታት ስራዎች ይከናወናሉ ብለዋል።
የሰመራ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት መሀመድ ኡስማን ( ዶ/ር)፤ የቱሪዝም ዘርፉ የሀገሪቱ ኢኮኖሚ የዕድገት ሞተር በመሆኑ ለውጤታማነቱ ሚናችንን እንወጣለን ብለዋል።
ቱሪዝምን የሚደግፉ የጥናትና ምርምር፣ የስልጠናና የቴክኖሎጂ ሽግግር ሥራዎችን በማጎልበት የሀገርን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እንደሚሠሩም ተናግረዋል።
የደባርቅ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት አስማማው ዘገየ (ዶ/ር)፤ የራስ ዳሽንና የዳሎልን አካባቢ እምቅ የተፈጥሮ ሀብቶችን በጥናትና ምርምር የመጠበቅና የመንከባከብ እንዲሁም በቴክኖሎጂ የመደገፍ ሥራዎች እንደሚከናወኑ ገልጸዋል።
የአካባቢውን ሕዝብ ለዓመታት የዘለቁ ማህበራዊ ትስስሮችን እንዲሁም የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያሳድጉ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አንስተዋል።