ቀጥታ፡

አስተዳደሩ ለልማት ተነሺዎች ያስገነባቸውን የመኖሪያ ቤቶች አስረከበ

ጅማ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦የጅማ ከተማ አስተዳደር ለልማት ተነሺዎች ያስገነባውን 300 መኖሪያ ቤቶች አስረከበ።

በመኖሪያ ቤቶቹ የርክክብ ስነስርዓት ላይ የክልል እና የዞን እንዲሁም የከተማ አስተዳደሩ የሥራ አመራሮች ተገኝተዋል።

የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ሀላፊ አቶ ጌቱ ገመቹ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፤ በክልሉ በርካቶችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የልማት ፕሮጀክቶች እየተከናወኑ ይገኛሉ።


 

ለዚህም በከተማ ብቻ ሳይሆን በገጠር የተጀመሩ የኮሪደር ልማት ሥራዎችም ምሳሌ ይሆናሉ ብለዋል።

ህዝብን ተጠቃሚ ለማድረግ የተቀረጹ ኢኒሼቲቮች እየተተገበሩ ይገኛሉ ያሉት አቶ ጌቱ ፣ በግብርና ዘርፍ፣ በመሠረተ ልማት  እና በሌሎችም የልማት ሥራዎች ስኬታማ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አመልክተዋል።

ለኮሪደር ልማት ማህበረሰቡ እያደረገው ያለው ትብብር የሚደነቅ መሆኑን ገልጸው፣ ሁሉም ልማቶች ለህዝብና ለሀገር ፋይዳቸው የጎላ በመሆናቸው ይጠናከራሉ ብለዋል፡፡


 

በተለይ በገጠር እና በከተማ ህዝብን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ በትኩረት ይሰራል ብለዋል።

የጅማ ከተማ ከንቲባ ጠሀ ቀመር፤ በከተማው በርካታ ፕሮጀክቶች በመንግስት እየተከናወኑ እንደሆኑና የተጠናቀቁትም ለአገልግሎት ክፍት እየተደረጉ ይገኛሉ ብለዋል።


 

በከተማዋ በዚህ አመት 80 የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸውን ጠቅሰው ዛሬ ለልማት ተነሺዎች ተገንብተው የተላለፉ መኖሪያ ቤቶች የዚሁ አንድ አካል ናቸው ብለዋል።

እነዚህ መኖሪያ ቤቶች ከ700 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸው ሲሆን ለ300 አባወራዎች ተላልፈዋል ብለዋል።

ከዚህን ቀደም በጅሬን፣ በቆፌ እና በሌሎችም የከተማዋ ቀበሌዎች የተገነቡ የተለያዩ መኖሪያ ቤቶች ለነዋሪዎች መሰጠታቸውንም አስታውሰዋል። 

ዛሬ የመኖሪያ ቤት ከተሰጣቸው የልማት ተነሺዎች መካከል  ሀጂ ሻፊ አባ ጉምቡል፤ የከተማ አስተዳደሩ በገባው ቃል መሠረት ምቹ የመኖሪያ ቤት ስላገኘን ደስተኞች ነን ብለዋል።


 

ወደፊትም ከመንግስት ጋር በመሆን ለልማት ሥራዎች የሚያደርጉትን ትብብር አጠናክረው እንደሚቀጥሉም ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም