ቀጥታ፡

የፌዴራል ተቋማት ተንቀሳቃሽ የመሶብ አገልግሎት፤ ይበልጥ ተደራሽና ቀልጣፋ በመሆን የደንበኞችን እርካታ ያረጋግጣል

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 26/2018 (ኢዜአ)፦ የፌዴራል ተቋማት ተንቀሳቃሽ የመሶብ አገልግሎት፤ የአገልግሎት አሰጣጡን ይበልጥ ተደራሽና ቀልጣፋ በማድረግ የደንበኞችን እርካታ በከፍተኛ ደረጃ የሚያረጋግጥ መሆኑን የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎችና ባለሙያዎች ገለጹ።

አገልግሎት አሰጣጡን ይበልጥ ቀልጣፋ፣ ተደራሽ እና ጥራት ያለው ለማድረግ የፌዴራል ተቋማት ተንቀሳቃሽ የመሶብ አገልግሎት ወደ ሥራ ገብቷል፡፡

ለማኅበረሰቡ ይበልጥ ተደራሽ በመሆን ወደ አገልግሎት የገቡት ሁለት ዘመናዊ ተንቀሳቃሽ ባሶች ቴክኖሎጂዎቻቸው ለአካባቢ ጥበቃ ትኩረት የሰጡ ናቸው፡፡

በዚህም አንደኛው ባስ ሙሉ በሙሉ በኤሌክትሪክ (EV) የሚሠራ ሲሆን ሁለተኛው የተፈጥሮ ጋዝን በመጠቀም የሚንቀሳቀስና አገልግሎት የሚሰጥ ነው፡፡

እነዚህ ተንቀሳቃሽ መስኮቶች የስድስት ቁልፍ የፌዴራል ተቋማትን አገልግሎቶች የሚሰጡ ሲሆን፣ አገልግሎቶቹም ተገልጋዮች ባሉበት ቦታ በመሄድ የተቀላጠፈ አገልግሎት የሚሰጡ ናቸው፡፡

ኢዜአ ያነጋገራቸው ተጠቃሚዎች እንደገለጹት፤ ተንቀሳቃሽ የመሶብ አገልግሎት እጅግ ፈጣን፣ ቀልጣፋና ምቹ አገልግሎት በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲያገኟቸው ማስቻሉን ጠቅሰዋል፡፡

አቶ በኃይሉ ወርቁ በሰጡት አስተያየትም ተንቀሳቃሽ የመሶብ አገልግሎት ማኅበረሰቡ ባለበት ቦታ ሆኖ ፈጣንና የተቀላጠፈ የመንግሥት አገልግሎት እንዲያገኝ ማስቻሉን ገልጸዋል።


 

ይህ የዲጂታል ትግበራ አገልግሎቱን ሙሉ በሙሉ ከሙስና የጸዳ፣ ግልጽና ተደራሽ በማድረግ ረገድ ከፍተኛ እገዛ እያደረገ መሆኑንም አክለዋል።

አቶ አስቻለው ጓዴ በበኩላቸው ተንቀሳቃሽ የመሶብ አገልግሎት በየአካባቢው እየተዘዋወረ አገልግሎት መስጠቱ ማኅበረሰቡን ከተጨማሪ ወጪና ከተንዛዛ እንግልት እንደታደጋቸው ገልጸዋል።


 

አሠራሩ ጊዜና ገንዘብን በአግባቡ ለመቆጠብ ያስቻለ በመሆኑም የተሰማቸውን ከፍተኛ ደስታ ገልጸዋል፡፡

በወረፋና በተለያዩ ቦታዎች መጉላላት ሳይኖር፣ በአንድ ማዕከል በርካታ አገልግሎቶችን ማግኘት መቻሉ ጊዜንና ጉልበትን በከፍተኛ ደረጃ እየቆጠበላቸው መሆኑን የገለጹት ደግሞ ወይዘሮ ወርቅነሽ እሸቱ ናቸው፡፡


 

የአገልግሎቱ ዲጂታላይዝ መሆን ከተገልጋዩ ባሻገር ለባለሙያዎችም የላቀ የሥራ ተነሳሽነትና ምቹ የሥራ አካባቢ መፍጠሩን አገልግሎቱን የሚሰጡ ባለሙያዎች ገልጸዋል፡፡

የአገልግሎቱ ባለሙያ አቶ አሰግድ ንዋይ እንደገለጹት፣ አዲሱ አሠራር ተቋማትና ባለሙያዎች ወደ ተገልጋዩ ይበልጥ እንዲቀራረቡና ግልጽነት የሰፈነበት አገልግሎት እንዲሰጡ አስችሏል።


 

 

እሌኒ ውድነህ በበኩሏ፤ አዲሱ የዲጂታል አሠራር ለሠራተኞች ጤናማ የሥራ ድባብ ከመፍጠሩም በላይ፣ የተገልጋዮች እርካታ ለባለሙያው ትልቅ መነሳሳት መሆኑን ጠቁማ፣ ተንቀሳቃሽ መሶብ ማኅበረሰቡን በእጅጉ ማስደሰቱን ገልጻለች።


 

የፌደራል መሶብ አገልግሎት ማዕከል ምክትል ኦፕሬሽናል ዘርፍ ኃላፊ ቤዛዊት ብርሃኔ በበኩላቸው፤ ይህ ዘመናዊ አሠራር ኅብረተሰቡ የመንግሥት አገልግሎቶችን ሁልጊዜም በታላቅ እምነት፣ ምቾትና አስተማማኝ በሆነ መልኩ እንዲያገኝ በር የከፈተ መሆኑን አረጋግጠዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም