ቀጥታ፡

በገጠር ኮሪደር፣በፍራፍሬ ልማትና በአግሮ-ኢንዱስትሪ የተጀመሩ ተግባራት ተስፋ ሰጪ ናቸው-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)

አዲስ አበባ፤ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ)፡- በገጠር ኮሪደር እና የፍራፍሬ ምርትን በአግሮ-ኢንዱስትሪ በማቀነባበር እሴት የተጨመረበት ምርት ወደ ገበያ ለማቅረብ የተጀመሩ ተግባራት ተስፋ ሰጪ ናቸው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለፁ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በጋሞ ዞን ምዕራብ አባያ ወረዳ እየተከናወነ ያለውን የገጠር ኮሪደር ልማት እና ሌሎች የልማት ሥራዎችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጉብኝታቸው ወቅት በገጠር ኮሪደር፣ በግብርና እና በኢንዱስትሪ ዘርፍ የተመዘገቡ ስኬቶችን አስመልክተው ማብራሪያ ሰጥተዋል።

ባለፈው ዓመት በመንግስት በኩል ሞዴል መንደሮችን መገንባቱን አስታውሰው፥ አርሶ አደሩ ሞዴል መንደሮችን በራሱ አቅም እንዲገነባ ማበረታቻ ሲደረግ እንደነበር አስታውሰዋል።


 

ዘንድሮ በምዕራብ አባያ ወረዳ የታዩት የገጠር ኮሪደር ሥራዎች ሙሉ በሙሉ በአርሶ አደሩ አቅምና ወጪ የተገነቡ መሆናቸውን ገልጸዋል።

መንግስት የማሰልጠን እና የጡብ ማሽነሪዎችን የማቅረብ ድጋፍ ብቻ ማድረጉን ጠቁመው፥ አርሶ አደሮች ከሙዝ ሽያጭ ባገኙት ገቢ ዘመናዊና ምቹ ቤቶችን መገንባት መቻላቸውን አድንቀዋል።

እነዚህ አዳዲስ የገጠር ኮሪደር ቤቶች የኤሌክትሪክ መብራትና ሌሎችም መሠረተ ልማቶች ያላቸው ሲሆን በጓሯቸውም ፍራፍሬ፣ ዶሮ፣ አሳ፣ ማርና የእንስሳት እርባታን ያካተቱ ናቸው ብለዋል።

ይህም አርሶ አደሩ ንጹህ ኑሮ እንዲኖር የሚያስችል፣የምግብ ዋስትናንና ጤናን የሚያረጋግጥ መሆኑን ተናግረዋል።


 

ይህ ሥራ የዜጎችን ህይወትና የአኗኗር ዘይቤን ይቀይራል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ በሁሉም አካባቢ ሲስፋፋ ኢትዮጵያን ወደ ምናስበው ከፍታ የመውሰድ አቅም አለው ብለዋል።

በአርባ ምንጭ አካባቢ የፍራፍሬ ማቀነባበሪያ ፋብሪካዎች ግንባታ መጀመሩን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ እነዚህ ፋብሪካዎች ማቀነባበር ሲጀምሩ ፍራፍሬዎችን በጥሬው ከመላክ ባለፈ የጭማቂ ምርቶችን ለገበያ በስፋት ማቅረብ እንደሚያስችሉ ተናግረዋል።

በተጨማሪም በሌማት ትሩፋት ዘርፍ የእርጎና ወተት ማቀነባበሪያዎች ስራ ሲጀምሩ ምርቶቹን እሴት ጨምሮ ወደ ከተሞች ለማቅረብ ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥሩ ገልጸዋል።

በግብርና፣ በገጠር ኮሪደር እና የፍራፍሬ ምርትን ከአግሮ-ኢንዱስትሪ ለማስተሳሰርና እሴት ለመጨመር እየተደረጉ ያሉ ሙከራዎች ተስፋ ሰጪ መሆናቸውን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቅሰዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም